የቡና ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር በማድረግ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ
ሀዋሳ፡ መጋቢት 01/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቡና ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር የሚረዱ ዘመናዊ ሥራዎችን ተግባራዊ በማድረግ ከዘርፉ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆናቸውን በወላይታ ዞን በቦሎሶ ሶሬ ወረዳ ነዋሪ የሆኑ አርሶ አደሮች ተናገሩ፡፡
በተያዘው የምርት ዘመን ከ160 ሄክታር በላይ መሬት የቡና ጉንደላ ሥራ ለማከናወን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን በወረዳው ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ጽህፈት ቤት አስታውቋል፡፡
ቡና ለአገራችን የኢኮኖሚ ዋልታ በመሆኑ ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ የውጭ ምንዛሪን ከማስገኘት ረገድ ትልቁን ሚና እየተጫወተ መሆኑ ተመላክቷል።
አቶ ክፍሌ ደምሴ እና አቶ ደምሴ ደስታ በቦሎሶ ሶሬ ወረዳ በአቹራ ማዘጋጃ የመብራት ኃይል መንደር ነዋሪዎች ሲሆኑ፥ ለበርካታ ዓመታት የተሻለ ምርት ይሰጥ የነበረ ቡና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ምርት እየቀነሰ በመምጣቱ የቡና ጉንደላ እንዲከናወን ማድረጋቸውን ተናግረዋል።
ለዚህም የግብርና ባለሙያዎች ድጋፍና እገዛ እንዳልተለያቸው የገለጹት አርሶ አደሮቹ፥ የተጎነደሉ ቡናዎች አቆጥቁጠው ፍሬ እስከሚሰጡ ድረስ አስፈላጊውን እንክብካቤ ሁሉ እንደሚያደርጉና ከዚህም የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ጠቁመዋል።
ምርት የማይሰጡ እና ረዥም ዓመት ያስቆጠሩ የቡና ተክሎችን በመለየትና ለምርታማነቱ ለአርሶ አደሩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቶችን በመስጠት ድጋፍና ክትትል እያደረጉ መሆናቸውን በአቹራ ማዘጋጃ የግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንድሙ ወጋየሁ አስረድተዋል።
አርሶ አደሩ ያለውን አነስተኛ መሬት በአግባቡ በመጠቀም የወቅቱን የኑሮ ጫናን ለመቋቋም እንዲችል የማስተባበርና የማስተማር ሥራዎች እየሰሩ መሆኑን የአቹራ ማዘጋጃ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋዬ ጌታቸው ገልፃዋል።
በተያዘው የምርት ዘመን ከ160 ሄክታር በላይ መሬት የቡና ጉንደላ ሥራ ለማከናወን ከታቀደው እስካሁን 95 በመቶ ተግባራዊ ማድረግ መቻሉን በወረዳው ቡና እና ቅመማቅመም ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አግዴ አሽኮ ተናግረዋል።
ዘጋቢ: ፍቃዱ ማቴዎስ – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
የሀለባ ዞን ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት ከ3 ቢልዮን 293 ሚልዮን ብር ባለይ በጀት አጸደቀ
መስራት እየቻሉ የገንዘብ እጥረት የገጠማቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን ችግሮች ለመፍታት የህብረት ስራ ማህበራት ሚና ቀላል አለመሆኑ ተገለጸ
በስልጤ ልማት ማህበር ለ3ኛ ጊዜ በተዘጋጀው የችግኝ ተከላ መርሀግብር ከሀገር ውስጥና ከውጪ ሀገር የተሰበሰቡ የአካባቢው ተወላጆች በዞኑ በሚገኙ የላንፉሮ ወረዳና ጦራ ከተማ አስተዳደር ችግኞችን ተክለዋል ።