በደቡብ ኦሞ ዞን በሣላማጎ ወረዳ በሌማት ትሩፋት በቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ኘሮጀክት ድጋፍ በዶሮ እርባታ ልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ተናገሩ
በሣላማጎ ወረዳ በጽጽማ ቀበሌ የሚገኙ አርሶ አደሮች ከሌማት ትርፋት ተግባር አንዱ በሆነው በዶሮ እርባታና እንቁላል ልማት ተጠቃሚ እየሆኑ ነው።
በወረዳው በጽጽማ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ወ/ሮ አሸቴ ኩስዬ በቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ኘሮጀክት ድጋፍ 24 ዶሮዎችን በማርባት ተጠቃሚ መሆን ችለዋል።
ወ/ሮ አሸቴ ጨምረው እንደገለፁት፤ ባገኙት ድጋፍ ሰርተው በ6 ወር ውስጥ በእንቁላል ሽያጭ ብቻ 23,800 ብር መቆጠብ መቻላቸውን ገልፀው በዚህም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጣቸውን አስታውቀዋል።
የቀበሌው ስራ አስኪያጅ አቶ ካሣዬ ገንድሻ፤ የወረዳው መንግስትና የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ኘሮጀክት ብሎም ግብርና ጽህፈት ቤት ላደረጉት ድጋፍና ክትትል አመስግነዋል።
በቀጣይም ሥራውን በቀበሌው በማስፋት እንደሚሰሩ ገልፀው፥ ምርቱን በፈለግነው ልክ እንዳናሳድግ በሽታ መከላከሉ ላይ በቅንጅት እንዲሰራ ሥራ አስኪያጁ ጠይቀዋል።
የሣላማጎ ወረዳ ግርብርና ጽህፈት ቤት እንስሳትና አሳ ሀብት ኤክስቴንሽን ቡድን መሪ አቶ ከተማ ካሳሁን እንደገለጹት፤ በወረዳው የተለያዩ የሌማት ትሩፋት መንደሮችን በማደራጀት እየተሰራ ሲሆን በዶሮ መንደር 3 ታቅዶ 11፣ በማር መንደር 5 ታቅዶ 6፣ በሥጋ መንደር 4 ታቅዶ 5 ማከናወን ተችሏል።
በተመሳሳይ መንግስት እንደ ሀገር የምግብ ዋስትና የሚረጋገጠው የቤተሰብ ብልፅግና ሲረጋገጥ እንደሆነ ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተግባሩን በተለየ ሁኔታ በመደገፍ በሌሎችም ዘርፎች ድጋፍና ክትትሉን በቀጣይነት በማጠናከር እየተሰራ እንዳለ ቡድን መሪው ገልፀዋል።
የሣላማጎ ወረዳ ግርብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ቶማስ አስካም በበኩላቸው፤ በወረዳው በሁሉም ቀበሌ በሌማት ትሩፋት አርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ ከተለያዩ አጋር አካላት ጋር በቅንጅት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም የቁጠባ ባህልን እንዲያሳድጉ በማስገንዘብ እና ምርጥ ተሞክሮዎችን በማስፋት እየተሰራ ሲሆን ሁሉም የቀበሌው ነዋሪ ተግባሩን በማጠናከር የቤተሰብ ብልፅግናን ለማረጋገጥ እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ዘጋቢ: ከተማ በየነ – ከጂንካ ጣቢያችን
በደቡብ ኦሞ ዞን በሣላማጎ ወረዳ በሌማት ትሩፋት በቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ኘሮጀክት ድጋፍ በዶሮ እርባታ ልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ተናገሩ

More Stories
በጎፋ ዞን ከ950 ቶን በላይ የብረት ማዕድን ክምችት መኖሩ ተገለጸ
በክልሉ የሚከናውኑ የመሠረተ ልማት ሥራዎች የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሊሆኑ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ገለፁ
የአፈርና ውሃ ጥበቃ በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ መስራት እንደሚገባ ተገለፀ