“ጠንካራ የመረጃ አያያዝ ሥርዓት የትምህርት ጥራትን ያስጠብቃል“ – ደስታ ገነሜ (ዶ/ር)
ሀዋሳ፡ መጋቢት 09/2018 ዓ/ም (ደሬቴድ) ጠንካራ የመረጃ አያያዝ ሥርዓት የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ሚናው የጎላ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ትምህርት ቢሮ አስታወቀ።
ቢሮው በትምህርት አስተዳደር መረጃ ሥርዓት ዲጂታላይዜሽን ላይ ያተኮረ የግምገማ መድረክ እያካሄደ ነው።
የመድረኩ ዓላማ የትምህርት መረጃ አስተዳደር ዘርፉን በመገምገም ቀጣይ አቅጣጫ ማስቀመጥ መሆኑ ተመላክቷል።
የቢሮው ምክትልና የመማር ማስተማር ዘርፍ ኃላፊ ደስታ ገነሜ (ዶ/ር)፥ በመክፈቻ ንግግራቸው ጥራት ያለው የመረጃ አያያዝ ሥርዓት የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል።
ባለፉት ጊዜያት የትምህርት መረጃ ሥርዓትን ለማዘመን በተደረገው ጥረት አበረታች ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመው፥ የትምህርት መረጃ በአግባቡ ከተሞላ የትምህርት ቤቶችን ሀብት ለመጠበቅ እንዲሁም ውስጣዊ ብቃት ለመለካት ያስችላል ነው ያሉት።
የትምህርት መረጃዎች በበይነ-መረብ ፖርታል ላይ የሚሞሉ መሆናቸውን ገልጸው፥ ባለድርሻ አካላት በአግባቡ እንዲሞሉ አሳስበዋል።
በክልሉ ይህ አሰራር ከተጀመረ ወዲህ አንዳንድ አከባቢዎች የጎልማሶች መሠረታዊ ትምህርት መረጃ፣ የመምህራን እና ሌሎች መረጃዎች በአግባቡ ያለመሞላት ችግር በዘርፉ የታዩ ክፍተቶች ናቸው ብለዋል።
በቀጣይ መሰል ችግሮችን በመፍታት መረጃዎችን በአግባቡ ፖርታል ላይ መሙላት ከባለድርሻ አካላት የሚጠበቅ ተግባር መሆኑን አመላክተዋል።
በቢሮው ባለሙያ አቶ ታጠቅ ታደሠ በኩል የአፈጻጸም ሪፖርት እየቀረበ ሲሆን፥ በቀጣይ በሪፖርቱ ዙሪያ በጥልቀት ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል።
ዘጋቢ፡ ሀብታሙ ኃይሌ – ከቦንጋ ጣቢያችን

More Stories
የኢትዮጵያ ህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም በጋሞ ዞን የተፈጥሮ አደጋ ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የገንዘብ ድጋፍ አደረገ
የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መስራት እንዳለባቸዉ ተገለፀ
በጋሞ ዞን በመሬት መንሸራተት አደጋ ለተጎዱ ወገኖች የአርባ ምንጭ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ፣ የአርባ ምንጭ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ እና የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን አርባ ምንጭ ቅርንጫፍ በጋራ በመሆን ከ300 ሺህ ብር በላይ የሚገመት የዓይነት ድጋፍ አደረጉ