በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ከ12 ቢሊየን ብር በላይ በጀት 471 ኪሎ ሜትር የአስፓልት መንገድ እየተሰራ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር አስታወቀ

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ከ12 ቢሊየን ብር በላይ በጀት 471 ኪሎ ሜትር የአስፓልት መንገድ እየተሰራ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር አስታወቀ

የመንገድ መሠረተ ልማቶቹ በተለያዩ ምክንያቶች የዘገዩ ቢሆንም በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቅ ክትትል እየተደረገ መሆኑንም የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ገልጿል።

በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የሚዛን አካባቢ ኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶች ማኔጅመንት ጽ/ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ጥላዬ ንጋቱ እንደገለፁት፤ አስተዳደሩ የመንገዶችን ጥራትና የኮንስትራክሽን ሂደትን በቅርቡ ለመከታተል ጽህፈት ቤቶችን በተመረጡ አካባቢዎች ከፍቶ እየሰራ ይገኛል።

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል በቤንች ሸኮ ዞን የሚዛን አካባቢ ኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶች ማኔጅመንት ጽ/ቤት በስሩ 6 ፕሮጀክቶች የሚዛን ቴፒ፣ የሺሻኤንዳ ቴፒ፣ ጎሬ ማሻ፣ ኩቢጦ ማዞሪያ እና መቱ ከተማ ውስጥ የሚከናወኑ የአስፓልት መንገዶች እንደሚገኙበት ስራ አስኪያጁ ገልፀዋል።

በክልሉ ከ12 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት እየተከናወነ ከሚገኘው የ471 ኪሎ ሜትር የአስፓልት መንገድ ሥራ የሚዛን ቴፒ አንዱና ከተጀመረ ረዘም ያለ ጊዜን የወሰደ በፀጥታ የንብረት ካሳ ክፍያ ከ3ኛ ወገን ነፃ ያለማደረግ ችግሮች በፕሮጀክቱ ላይ ተፅዕኖ ማሳደራቸውን አቶ ጥላዬ አብራርተዋል።

እንዲሁም የተለያዩ የዕቃዎችና የማሽነሪ ዋጋዎች ንረትን በመቋቋም ከኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣንና ከቻይና ሀገር ኮንትራክተር ተወካዮች ጋር በመወያየት አስፈላጊውን የስራ አቅጣጫ በማስቀመጥ ፕሮጀክቱ በጥሩ መሻሻል ላይ እንደሚገኝ ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል።

አካባቢው ዝናባማ በመሆኑ ያለውን አጭር ጊዜ ለመጠቀም ርብርብ እየተደረገ ሲሆን እስካሁን ባለው ከሚዛን ቴፒ 48 ኪሎ ሜትር የአምናውን ጨምሮ 15 ኪሎ ሜትር መንገድ አስፓልት በማልበስ ወደ 20 ኪሎ ሜትር ለማድረስ እየተሰራ ነው ብለዋል።

የጎሬ ማሻ በዚህ በጀት ዓመት 20 ኪሎ ሜትር የተከናወነ ሲሆን ወደ 50 ኪሎ ሜትር ለማድረስ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ አቶ ጥላዬ ገልፀው፤ ለኮንትራክተሮች አስፈላጊውን ሲሚንቶ፣ ነዳጅ እንዲሁም የወሰን ማስከበር ተግባራት በትኩረት ሊሰራ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በአስፓልት መንገድ ግንባታው የየኪ፣ የሸኮ ወረዳዎችና የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደሮች እያገዟቸው እንደሆነ የገለፁት አቶ ጥላዬ፤ ፕሮጀክቱን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በአዲሱ አዋጅ መሠረት የወሰን ማስከበር ስራዎችን የሚመለከታቸው አካላት የተሰጣቸውን ድርሻ በኃላፊነት ሊወጡ እንደሚገባ አብራርተዋል።

በሁሉም ፕሮጀክቶች ርብርብ እየተደረገ እንዳለ ያስታወሱት ስራ አስኪያጁ፤ የመንገድ መሠረተ ልማቱ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2026 በተያዘለት ጊዜ ለመጨረስ በተለይ በከተማ እየታየ ያለውን የወሰን ማስከበር ስራ የአካባቢውና የዞን አስተዳደሮች እንዲሁም የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር በሚጠበቀው ልክ ክትትል ከተደረገ ይጠናቀቃል ብለዋል።

ከችግሮች ጋር ተያይዞ ለአብዛኞቹ ኮንተራክተሮች ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው የቢሮ ኃላፊው ገልፀው፤ ከሚዛን ቴፒና ከቴፒ ማሻ ጎሬ ያለው የአስፓልት መንገድ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲጠናቀቅ የሚዛን ዲማ ደግሞ በቀጣይ እንዲጠገን ጥረት ይደረጋል ብለዋል።

የቻይና CCG ግሩፕ ኮንተራክተር ፕሮጀክት ማናጀር ሚስተር ዞ በበኩላቸው፤ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ጃንዋሪ 2018 የተጀመረው የአስፓልት መንገድ ፕሮጀክት ከአሰሪና ከኮንትራክተሮች ጋር ባጋጠመው ችግሮች እንደዘገየና አሁን በተደረገው ጥረት የሚዛን ቴፒ 60 ከመቶ በማጠናቀቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።

በዚህ ዓመት 20 ኪሎ ሜትር ለማጠናቀቅ አቅደው 12 ኪሎ ሜትር እንዳደረሱና ቀሪውን ለመጨረስ አስፈላጊውን ማሽኖች በመጨመር ርብርብ የሚደረግ ሲሆን የአካባቢው መስተዳድሮች ከወሰን ማስከበር ጀምሮ የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደረጉ አሰገንዘበዋል።

ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል ወጣት ጥላሁን ሽፈራው እና አቶ አበበ ፂኪያብ በሰጡት አስተያየት፤ መንገድ በመሰራቱ የትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቃሚ እንደሆኑና ተጀምረው ያልተጠናቀቁ በትኩረት እንዲሰራላቸው ጠይቀዋል።

ዘጋቢ፡ አብዲሳ ዮናስ – ከሚዛን ጣቢያችን