የመድሀኒት ተቋማት ስታንዳርድ ትግበራ የዳሰሳ ጥናት ውጤት ይፋ ማድረጊያ መርሀግብር ተካሄደ

ሀዋሳ፡ ሰኔ 18/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ የመድሀኒት ተቋማት ስታንዳርድ ትግበራ የዳሰሳ ጥናት ውጤት ይፋ ማድረጊያ መርሀግብር እየተካሄደ ይገኛል።

በመድረኩ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የኢትዮጵያ ምግብና መድሀኒት ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር ወ/ሪት ሄራን ገርባ፥ ኢትዮጵያ ከመድሀኒት ቁጥጥር ጋር በተያያዘ በአለም አቀፍ ደረጃ ሆነ በምስራቅ አፍሪካ የተሻለ የህግ ማዕቀፍ ካላቸው ሀገራት ተርታ ማሰለፏን አመላክተዋል፡፡

አግባባዊ የመድሀኒት አጠቃቀም እንዲኖር በመድሀኒት ችርቻሮ መደብሮች ወጥ ያልሆነ የፈቃድ አሰጣጥን በማስቀረት ተመሳሳይ የሆነ ህጋዊ እርምጃ መውሰድ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ም/ቢሮ ኃላፊና የጤናና ጤናነክ አገልግሎት ግብዓት ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ ፋሲካ አለሙ በበኩላቸው፥ በክልሉ ከ595 በላይ የመድኃኒት ችርቻሮ ተቋማት ላይ በተደረገ ጥናት ከደረጃ በታች የሆኑ መድሀኒቶችን ይዞ መገኘት፣ የግዢ ደረሰኝ አለመያዝ፣ ኮንትሮባንድና ከመንግስት ተቋማት የተሰረቁ መድኃኒቶችን መያዝ፣ ያለማዘዣ መሸጥና ሌሎች ችግሮች መስተዋሉን ጠቁመው፥ ይህንን ለማስቀረት ከጠያቂነት ባለፈ ህብረተሰብ ተኮር ስራን መስራት ያስፈልጋል ተብለዋል።

የምስራቅ ጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ጉግሳ በበኩላቸው፥ በዞኑ የግል መድሀኒት ችርቻሮ ተቋማት የውስጥ ጥራት ቁጥጥር 90% መድረሱን ጠቅሰው፥ ስታንዳርዱን ላሟሉ መድሀኒት ቤቶች ማበረታቻ በመስጠት ህጉን ተግባራዊ ያላደረጉ ተቋማትን ማስተማርና ማረም መቻላቸውን ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ ራሔል አሊ