ምርታማነትን የሚያሳድጉ የግብርና ቴክኖሎጂዎች በወቅቱ እንዲቀርቡ ተጠየቀ
ሀዋሳ፡ ጥር 14/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ምርታማነትን የሚያሳድጉ የግብርና ቴክኖሎጂዎች በወቅቱ እንዲቀርቡላቸው በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የቀበሌ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊዎች ጠየቁ።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ለቀበሌ ግብርና ጽ/ቤት ኃላፊዎች ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ለሚደረገው ሽግግር የቤተሰብ ኑሮ ማሻሻያ ፖኬጆች ላይ በጂንካ ማዕከል ለሦስት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የነበረው ስልጠና ተጠናቋል።
በላፉት ሦስት ቀናት በግብርናው ዘርፍ በተለይም በሰብል፣ በፍራፍሬና አትክልት፣ በእንስሳት ምርታማነት፣ በአፈርና ውሃ ጥበቃ እንዲሁም በሌሎች የግብርና ፖኬጆች ስልጠናው ሲሰጥ ቆይቷል።
የስልጠናው ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ስልጠናው በየአካባቢያቸው የጀመሩትን የልማት ስራዎችን ለማስቀጠል አቅም እንደፈጠረላቸው ገልፀዋል።
በቀጣይ መሰል የግንዛቤ መድረኮች ተጠናክረው እንዲቀጥሉና ምርታማነትን ለማሳደግ የግብርና ቴክኖሎጂዎች እንዲቀርቡላቸው ጠይቀዋል።
ስልጠናውን የሰጡ አካላትም በጽንሰ ሐሳብ ደረጃ ለተነሱ ጥያቄና አስተያየቶች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የእንስሳት ጤና እና ግብዓት አቅራቦት ዘርፍ ኃላፊና የጂንካ ስልጠና ማዕከል አስተባባሪ ዶ/ር አድሱ ኢዮብ፤ በክልሉ አብዛኛው አካባቢ የተጀመሩ የምርት ስራዎችን በማሳደግ የአርሶና አርብቶ አደሩን ምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ የገበያ ፍላጎቱን ለማርካት ምርታማነትን የሚያሳድጉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን አብዝቶ መጠቀም ይገባል ብለዋል።
ከቴክኖሎጂ በተጨማሪ በክልሉ ያሉ የውሃ ሀብቶችን አሟጦ በመጠቀም ማህበረሰቡን ከዝናብ ጥገኝነት ማላቀቅና ምርታማነትን ለማሳደግ በተዋረድ ያሉ የግብርና መዋቅሮች እንዲሰሩ አሳስበዋል።
ምርታማነትን ለማሳደግ በክልሉ የተለያዩ አካላት በድጋፍ የሚቀርቡ ልዩ ልዩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ ጠብቆ መጠቀም ያስፈልጋል ያሉት ዶ/ር አድሱ፤ መሰል ድጋፎችን በቀጣይ ክልሉ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
ዘጋቢ፡ መልካሙ ቡርዝዳቦ – ከጂንካ ጣቢያችን

More Stories
ማሳቸውን ለመኸር እርሻ ደጋግማው በማረስ አለስልሰው በወቅቱ ለመዝራት መዘጋጀታቸውን በከምባታ ዞን ቀዲዳ ጋሜላ ወረዳ ያነጋገርናቸው አንዳንድ አርሶአደሮች ተናገሩ
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በተለያዩ የስራ ዘርፎች ከ40 ሺህ በላይ ወጣቶችን ተሳታፊ በማድረግ 46 ሚሊዮን 620 ሺህ ብር በላይ ከመንግሥት ሊወጣ የሚችለውን ለማዳን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ጽ/ቤት አስታወቀ
የቀቤና ልዩ ወረዳ ማህበረሰብ የልማት ፍላጎት ማሟላት የሚቻለው ግብርና ታክስ በታማኝነትና በወቅቱ መክፈል ሲቻል መሆኑ ተገለጸ