በ75 ሄክታር መሬት ላይ እየለማ ያለ የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት ቴክኖሎጂ ማስተዋወቅና የተግባር መስክ ምልከታ ተካሔደ
ሀዋሳ፡ ታህሳስ 22/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በአሪ ዞን ሰሜን አሪ ወረዳ በ75 ሄክታር መሬት ላይ እየለማ ያለ የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት ቴክኖሎጂ ለማስተዋወቅና የተግባር መስክ ምልከታ መካሔዱ ተገለጸ፡፡
የጅንካ ግብርና ምርምር ማዕከልና የሰብል ዝርያ ማሻሻያ ከፍተኛ ተመራማርና የማዕከሉ ዳይሬክተር ዶ/ር ተክሌ ዮሰፋ እንደገለፁት፥ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ 14 ዓይነት የስንዴ ዘር ሙከራ በማድረግ ከአከባቢው ጋር ተስማሚ የሆነውን የ‘ኦኮልቾ’ ስንዴ ዝርያ በማባዛት ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል።
በወረዳው ሻንጋማ ፃክ እና ማጣ ዛብር ቀበሌ እየለማ የሚገኘው 75 ሔክታር የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት፥ 164 አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ጠቁመው፥ ከአንድ ጥማድ ማሳ ከአራት ኩንታል በላይ እንደሚያገኙ የቀበሌው ሊቀመንበር ዮናስ እሸቱ እና አርሶ አደር ዳንኤል ሀይሌ ተናግረዋል።
የሰሜን አሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታፈሰ ተስፋዬ እንደገለጹት በምርምር የተገኙት የልማት ቱርፋቶች አበረታች በመሆኑ ለአርሶ አደሮች የግንዛቤ ስራ ማጠናከር እንደሚገባ ገልፀዋል።
የታየዉ የምርጥ ዘር ብዜት ለሁሉም ማህበረሰብ ሊዳረስ የሚገባና የታየው ውጤትም አበረታች መሆኑን የአሪ ዞን ዋና የመንግስት ተጠርና የብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ ገልፀዋል።
የኑሮ ውድነትንና የገበያ መረጋጋት ስራ ላይ የሃገራችን ጀርባ አጥንት የሆነዉን የግብርና ስራ በቴክኖሎጂ በማስደገፍ መስራት እንደሚጠበቅ የታየው ምርት አበረታች መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ተመስገን ንፍርቄ – ከጂንካ ጣቢያችን
More Stories
በኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሠማሩ የግል ባለሀብቶች ከመንግስት የተረኩቡትን ሀብት በተገቢው እንዲያለሙ ተጠየቀ
በዳዉሮ ዞን ታርጫ ከተማ የሚካሄዱ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ልማቶች አሁን ላይ ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አልማው ዘውዴ ገለጹ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በማር ምርት ዘርፍ 360 ሺህ ሥራ አጥ ወጣቶችን በማደራጀት ወደ ሥራ ለማስገባት እየተሠራ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር አበባየሁ ታደሰ አስታወቁ