የዋካ ከተማ አስተዳደር የባለ አደራ ምክር ቤት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት ለመጪው ገና በዓል ለእርድ የሚሆን የቁም ከብት በብዛት ለማቅረብ መዘጋጀቱን አስታወቀ
ሦስተኛ ሣምንቱን በያዘው የዋካ ቅዳሜ የቁም ከብት ገበያ ግብይቱ እንደበፊቶቹ ሣምንታት ሁሉ በደራ ሁኔታ ቀጥሏል።
በገበያው ሰንጋ በሬዎች ከሰላሳ እስከ ሃምሳ ሺህ ብር እየተሸጡ ያለ ሲሆን ሙክት በግና ፍየሎች ደግሞ ከአስራ አምስት እስከ ሃያ አምስት ሺህ በመገበያየት ላይ ነው የሚገኙት።
ከዚሁ ጎን ለጎን በገበያው ለመጪው ገና በዓል የሚሆኑ ሰንጋ በሬዎች እና ሙክት በግና ፍየሎችን ለሸማቾች በብዛት ለማቅረብ ከአቅራቢ ባለድርሻዎች ጋር በመሆን እየሰራን ነው ሲሉም የከተማዋ አስተዳደር ባለ አደራ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የሆኑት አቶ እስክንድር ተፈራ ተናግረዋል።
በገበያው አግኝተን ያነጋገርናቸው በርካታ ሻጭና ገዢዎች በሰጡት አስተያየት፣ ቅዳሜ ዕለት የሚቆመው ይኸው የዋካ ገበያ ከሣምንት ወደ ሣምንት እየደራ መሆኑን ገልጸው፣ ገበያው ገና ጅምር ላይ እንደመሆኑ በሁለት እግሩ እስኪቆም ድረስ ትርፍን መሠረት አድርገን ሳይሆን ለከተማዋ መልማት አጋዥ አንዲሆን ስንል በተለይ ገበያውን ለማጠናከር እንሰራለን ብለዋል።
ያነጋገርናቸው ሰንጋና ሙክት አቅራቢዎችም በቂ አቅርቦት ያለ መሆኑን አረጋግጠዋል።
ከተማዋን የበለጠ ለማልማት በቀጣይ ባዛር ለማዘጋጀት የባለ አደራ ምክር ቤቱ እቅድ መያዙንም አስታውቋል።
በእቅዱ መሠረት ባዛሩ ከጥር 3 እስከ 6/2017 ዓ.ም ባለው ጊዜ በዋካ ከተማ የሚደረግ ሲሆን በወቅቱ የልማት አጋሮች የሆኑት ሁሉ በመገኘት አጋርነታቸውን እንዲገልፁም የባለ አደራ ምክር ቤቱ ጥሪ አስተላልፏል።
ዘጋቢ፡ አሸናፊ ግዛው – ከዋካ ጣቢያችን

More Stories
በጎፋ ዞን ከ950 ቶን በላይ የብረት ማዕድን ክምችት መኖሩ ተገለጸ
በክልሉ የሚከናውኑ የመሠረተ ልማት ሥራዎች የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሊሆኑ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ገለፁ
የአፈርና ውሃ ጥበቃ በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ መስራት እንደሚገባ ተገለፀ