የወባ በሽታ ስርጭት ለመቀነስ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሚገኙ ተጠቆመ
ሀዋሳ፡ ሕዳር 17/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በተለያዩ አካባቢዎች ህብረተሰቡን ለጉዳት እየዳረገ የሚገኘውን የወባ በሽታ ስርጭት ለመቀነስ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሚገኙ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የጠምባሮ ልዩ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት አስታወቀ።
ውኃ ያቆሩ ጉዳጓዶችን በማፋሰስና ሌሎች የመከላከያ ተግባራት ቢከናወኑም፥ በጤና ተቋማት የመድኃኒት እጥረትና የአጎበር ተደራሽነት ክፍተት ትኩረት ሊሰጥበት ይገባል ሲሉ አንዳንድ የህብረተሰብ ክፍሎች ተናገሩ።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የጠምባሮ ልዩ ወረዳ ጤና ጽ/ቤት ኃላፊ ዶክተር ፀጋዬ ሻሜቦ በአብዛኛዎቹ የልዩ ወረዳው ቆላማ አካባቢዎች የበሽታው ስርጭት መኖሩን ጠቁመው የቁጥጥር ስራዎች በትኩረት እየተሰሩ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
የስርጭቱ ባህርይ ከወትሮ የተለየ መሆኑን የጠቆሙት ኃላፊው ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት በሚሰሩ የመከላከያ ስራዎች ለውጦች እየታዩ መሆናቸውን አመላክተዋል።
በልዩ ወረዳው ጤና ጽ/ቤት ምክትል ኃላፊና በሽታ መከላከል ዋና ስራ ሂደት አስተባባሪ አቶ አማረ በየነ በበኩላቸው ከበሽታው ቁጥጥር ስራዎች በተጨማሪ ለህብረተሰቡ በበሽታው ስርጭት ዙሪያ የግንዛቤ ስራዎች በስፋት እየተሰሩ ይገኛል ብለዋል።
ውኃ በሚያቁሩ አካባቢዎች የኬሚካል ርጭትና የማፋሰስ ስራዎች ብሎም አጎበር አጠቃቀም ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
በልዩ ወረዳው ያነጋገርናቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ውኃ ያቆሩ አካባቢዎችን በማፋሰስና ሌሎችንም የመከላከያ ጥንቃቄ ተግባራትን እያከናወኑ ቢሆንም በጤና ተቋማት አልፎ አልፎ የሚስተዋሉ የመድኃኒት እጥረትና የአጎበር ተደራሽነት ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ትኩረት ሊሰጥ ይገባል የሚል አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ዘጋቢ: አማኑኤል አጤቦ – ከሆሳዕና ጣቢያችን

More Stories
የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ በይፋ መጀመሩን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ህብረተሰብ ጤና ኢንስትቲዩት አስታወቀ
በኮሬ ዞን አራተኛ ዙር የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ በይፈ ተጀመረ
የጡት ካንሰር ተገቢው ህክምና በወቅቱ ካልተደረገ ለከፋ አደጋ የሚያጋልጥ እንደመሆኑ ድንገት ሲያጋጥም በባህል ህክምና ከመዘናጋት ይልቅ በአፋጠኝ ወደ ጤና ተቋማት መሄድ ተገቢ ነው – ዶክተር ተሾመ አለምቦ