መንግሥት የብሔረሰቦች ባህል፣ ቋንቋና መልካም ዕሴቶች እንዲታወቁና እንዲጎለብቱ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑ ተገለፀ

መንግሥት የብሔረሰቦች ባህል፣ ቋንቋና መልካም ዕሴቶች እንዲታወቁና እንዲጎለብቱ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑ ተገለፀ

የማጃንግ ብሔረሰብ የባህልና ቋንቋ ሲምፖዚየም ፓናል ውይይት በሸካ ዞን ቴፒ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል።

በሲምፖዚየሙ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የሸካ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ አበበ ማሞ እንደገለፁት፥ በፌደራሊዝም ሥርዓት ህብረብሔራዊ አንድነት እንዲጠናከርና የብሔረሰቦች እኩልነት እንዲረጋገጥ መንግሥት በልዩ ትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል።

በዚህም የብሔረሰቦች ባህል፣ ቋንቋና ታሪክ እንዲታወቅና እንዲለማ እየተሰራ ያለው ስራ ማሳያ መሆኑን የገለፁት ዋና አስተዳዳሪው፥ የማዣንግ ብሄረሰብ ባህል፣ ቋንቋ እና ታሪክ እንዲጎለብት የተጀመሩ ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ ጠቁመዋል።

የማጃንግ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዮናስ አበበ በበኩላቸው የማጃንግ ብሄረሰብ የራሱ የሆነ ባህል፣ ታሪክ፣ ቋንቋ እና መልካም ዕሴቶች ያሉት ብሄረሰብ መሆኑን ገልፀዋል ።

የቴፒ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ የሆኑት አቶ ገላትያ ሻሜ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልክት በማስተላለፍ የማጃንግ ብሄረሰብ ባህል፣ ቋንቋ እና መልካም ዕሴቶች እንዲለሙና እንዲጎለብት በትኩረት ይሰራል ሲሉ ተናግረዋል።

በሲምፖዚየሙ ላይ በብሔረሰቡ ቋንቋና ባህል ላይ ትኩረት ያደረጉ ጥናታዊ ፅሁፎች በክልሉ ብሄረሰቦች ምክር ቤት ፅ/ቤት ሃላፊ አቶ ተስፋዬ እንዳሻው እየቀረበ ሲሆን በቀረበው ሰነድ መነሻ ውይይቶች ይደረጋሉ።

በሲምፖዚየሙ ላይ የጋምቤላ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ መሠረት ማቴዎስ፣ የሸካ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አበበ ማሞን ጨምሮ ከጋምቤላ፣ ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የብሔረሰቡ ተወላጆችና ተጋባዥ እንግዶች፣ የዩኒቨርሲቲ ምሁራንና የሌሎችም ብሔረሰብ ተወካዮች እየተሳተፉ ነው ።

ዘጋቢ: አስቻለው አየለ – ከማሻ ጣቢያችን