በእንስሳት ሃብት ልማትና በእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች ላይ ትኩረት ያደረገ አውደ ርዕይ ሊካሄድ ነው
ሀዋሳ፡ ጥቅምት 13/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በእንስሳት ሃብት ልማትና በእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች ላይ ትኩረት ያደረገ አውደ ርዕይ እና ጉባኤ እንደሚካሄደ ተገለጸ።
አውደ ርዕይ እና ጉባኤው ለሦስት ተከታታይ ቀናት በአዲስ አበባ ሚሊኒየም አደራሽ እንደሚካሄድም ተጠቁሟል፡፡
በአውደ ርዕዩ ከ14 ሃገራት የተውጣጡ ከ100 በላይ ዓለም አቀፍ የእንስሳት ሃብት ዘርፍ ተዋናዮች እና የሀገር ውስጥ ባለድርሻ አካለት የሚሳተፉበት ይሆናል ተብሏል።
ከጥቅምት 21 እስከ 23 ቀን 2017 ዓ.ም ባሉት ሦስት ቀናት ውስጥ የሚካሄደው አውደ ርዕይ በግብርና ሚኒስቴር፣ በኢትዮጵያ እንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት፣ በኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን፣ በኔዘርላንድስ ልማት ድርጅት ፕሮግራም (ኤስ.ኤን.ቪ) እና በዓለም አቀፍ የነፍሳት ፊዚዮሎጂና ሥነ-ምህዳር ማዕከል (ICIPE) የሚዘጋጅ መሆኑን የንግድ ትርኢቱ አዘጋጅ የሆነው ፕራና ኤቨንትስ አስታውቋል።
የፕራና ኢቨንትስ መስራችና ዋና ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ነብዩ ለማ ከተባባሪዎቹ ጋር በመሆን በአጠቃላይ ዝግጅቱ ዙሪያ መግለጫ ሰጥተዋል።
በአውደ ርዕዩ ከቻይና፣ ከቼክ ሪፐብሊክ፣ ከኢትዮጵያ፣ ከፈረንሳይ፣ ከጀርመን፣ ከህንድ፣ ከኬኒያ፣ ከጆርዳን፣ ከኔዘርላንድስ፣ ከስኮትላንድ፣ ከቶጎ፣ ከቱርክ፣ ከዩጋንዳ እና ከአሜሪካ የእሴት ሰንሰለቱን የሚወክሉ የዘርፉ መሪዎችና የሀገር ውስጥ ኩባንያዎች ከንግድ ጎብኚዎች ጋር የስራ ግንኙነት ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል።
ከ5000 በላይ የኢትዮጵያ፣ የምስራቅ አፍሪካ እና ዓለም አቀፍ ሀገራት ጎብኚዎች እንደሚሳተፉም ተጠቁሟል።
ተሳታፊዎቹ በእንስሳት ሃብት ልማትና በእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች ላይ የገበያ ተስስር፣ የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር እንዲሁም የኢንቨስትመንት አማራጮችን የሚቃኙበትን ምቹ አጋጣሚ እንደሚፈጥርላቸውም በመግላጫው ተብራርቷል፡፡
በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና አሳ ሀብት ልማት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ጽጌሬዳ ፍቃዱ በበኩላቸው አወደ ርዕዩ የእንስሳት ዘርፉን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሌማት ትሩፋት ፕሮግራምን ጨምሮ በመንግሥት በኩል እየተተገበሩ ያሉ ተግባራትን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ የሚያግዙ ተሞክሮዎች የሚገኙበት ይሆናል ብለዋል።
በኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚደረገው ሁሉን አቀፍ ጥረት ውስጥ አዎንታዊ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክትም ተናግረዋል።
ዘጋቢ፡ ጌታሁን አንጭሶ

More Stories
ወጣቶች በዞኑ የሚገኙ ጸጋዎችን ተጠቅመው የገቢ አቅማቸውን እንዲያሳድጉ እየተደረገ ያለው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው የጉራጌ ዞን ምክር ቤት ገለጸ
በያዝነው ዓመት አስከ ጥቅምት ወር ድረስ 2 መቶ 50 ቶን በላይ ቡና ለማዕከላዊ ገበያ መላኩን የባስኬቶ ዞን ላስካ ዙሪያ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ
የምርምር ተቋማት ከዝናብ ጥገኝነት ተላቀው የግብርናውን ስራ ውጤታማ እንዲያደርጉ የመስኖ ፕሮጀክት ግንባታ ስራ አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ኢንስቲትዩት አስታወቀ