የፊቼ ጫምባላላ በዓል በሀዋሳ ከተማ በሲዳማ ባሕል አዳራሽ በድምቀት እየተከበረ ይገኛል
የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፥ የዛሬው ዕለት በሲዳማ አቆጣጠር አሮጌው ዘመን ተሸኝቶ አዲስ አመት የምንቀበልበት ነው ብለዋል፡፡
በሲዳማ አቆጣጠር አዲስ አመት የሚጀምረው አሮጌው ዓመት ፀሐይ ስትጠልቅ አዲሱ አመት የሚጀመርበት መሆኑን ጠቁመው፥ በአሉን ለማክበር የተለያዩ ዝግጅቶች በማድረግ በብዙ ሁነቶች ታጅቦ የሚከበርና ትልቅ ታሪክ ብሎም ባህል ያለው ነው ብለዋል፡፡
ስለሆነም ባለፈው ዓመት የተፈጠሩ መልካም ያልሁኑ ነገሮች የሚፈቱበት፣ መልካም የሆኑ ነገሮች የሚቀጥሉበት መሆኑን አመላክተው፥ የተጣሉ የሚታረቁበት፣ ያዘኑ የሚጽናኑበት አቅም የሌላቸው የሚደገፉበት ሲሆን የሰው ልጆች ተደስተው የሚያሳልፉት የደስታ በዓል ነው ብለዋል፡፡
አሁን ያለንበት ወቅት ከፊቼ ጫምባላላ ውስጥ “ፊቼ ቢጣላ” ማታ ላይ መገኘታቸውን ጠቁመው፥ “ቢጣላ” የሚባለው የፊቼ ጫምባላላ የመጀመሪያ ቀን ማታ እንደሆነ ጠቁመው በዚህ ቀን ሲዳማዎች ከፍተኛ ደስታቸውን የሚገልፁበት የሚጠጡበት፣ የሚበሉበት በጋራ የሚያሳልፉበት፣ የሚከባበሩበት ማምሻ ነው ብለዋል፡፡
ስለዚህ የሲዳማ አዲስ ዘመን 2019 ዓ.ም ከጥቂት ሰዓታት በኋላ በይፋ የሚጀመር መሆኑን አሳውቀዋል፡፡
ርዕሰ መስተዳድሩ አያይዘው እንደገለፁት፥ ያሳለፍንበት መንገድ በመርመር የአዲሱ አመት የተሻለ ነገር ፈጽሞ ለመገኘት እንዲሁም ያልተሳኩ ጉዳዮችን ወደስኬት በመቀየር ግጭቶችንና ቁርሾዎችን በመፍታት የሲዳማ አንድነት ተጠናክሮ ሁላችንም አዲሱን አመት ለተሻለ ስኬት ዝግጁ መሆናቸውን አመላክተዋል፡፡
አዲሱን አመት የምንቀበልበት ሂደት መጀመራችንን በይፋ አበስራለሁ ብለዋል፡፡
ዘጋቢ፡ ሐና በቀለ
የፊቼ ጫምባላላ በዓል በሀዋሳ ከተማ በሲዳማ ባሕል አዳራሽ በድምቀት እየተከበረ ይገኛል

More Stories
በወራቤ ዩኒቨርስቲ ሴቶችን ወደ አመራርነትና ውሳኔ ሰጪነት ለማምጣት ባለፉት አመታት በተከናወኑ ስራዎች ለውጦች እየተመዘገቡ መምጣታቸው ተመላከተ
50ኛው የኢትዮጵያ ሴቶች ቀን (ማርች 8) በዋቸሞ ዩኒቨርስቲ እየተከበረ ነው።
ሠላምን በሠላም ጊዜ እንደሚሠራ ተገለጸ