በባስኬቶ ዞን በመኸር የእርሻ ወቅት ከለማዉ 1 ሺህ 575 የጤፍ ማሳ ከ20 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሚሰበሰብ የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ
ከሰሞኑ እየጣለ ያለዉ ዝናብ የደረሰዉን የጤፍ ምርት እንዳያበላሽ አርሶ አደሮች ምርቱን ከማሳ የማንሳት ሥራ አጠናክረዉ እንዲቀጥሉ መምሪያው አሳስቧል።
በባስኬቶ ዞን በመኸር እርሻ ከ11 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በልዩ ልዩ ሰብሎች መሸፈን ተችሏል፡፡ ከዚህ ውስጥ 1ሺህ 575 ሄክታሩ በጤፍ ምርት የተሸፈነ መሆኑ ተመላክቷል።
በዞኑ ላስካ ዙሪያ ወረዳ በኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴ በማህበር ተደራጅተው ጤፍ ያመረቱ አርሶ አደሮች እንደተናገሩት የተጠቀሙት የጤፍ ዝርያ ከአካባቢው ጋር የተስማማ በመሆኑ የተሻለ ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል።
ያመረቱትን የጤፍ ምርት በወቅቱ ለገበያ አቅርበው በተሻለ ዋጋ እንዳይሸጡ በአካባቢው ከፍተኛ የመንገድ ችግር መኖሩንም አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል።
የባስኬቶ ዞን ግብርና መምሪያ ሰብል ዘርፍ ኃላፊ አቶ ዘላለም ኪዳኔ፤ በመኸር የእርሻ ወቅት ከለማዉ 1 ሺህ 575 የጤፍ ማሳ ከ20 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሚሰበሰብ ገልጸዋል።
የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ወንድአፍራሽ ንጉሤ፤ በመኸር የእርሻ ወቅት በተያዘው እቅድ መሠረት በሁሉም የሰብል አይነቶች የተሻለ ምርት መገኘቱን አብራርተዋል።
ከሰሞኑ እየጣለ ያለዉ ዝናብ በተለይ የደረሰዉን የጤፍ ምርት እንዳይጎዳው አርሶ አደሮች ምርቱን ከማሳ የማንሳት ሥራ አጠናክረዉ እንዲቀጥሉም አቶ ወንዳፍራሽ አሳስበዋል።
አርሶ አደሩ ያነሳው የመንገድ ችግር በመኸር ወቅት ብቻ ሳይሆን ባሳለፍነው በልግ የእርሻ ወቅት የተሰበሰበውን ምርት ለብልሽት እየዳረገው መሆኑን የመምሪያው ኃላፊ አንስተዋል።
የመንገድ ተደራሽነት ችግር ከዞኑ አቅም በላይ በመሆኑ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት አስፈላጊውን ርብርብ እንዲያደርጉ የባስኬቶ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ፍሬው ፍሻለው ጥሪ አቅርበዋል።
ዘጋቢ: አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን

More Stories
የሀለባ ዞን ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት ከ3 ቢልዮን 293 ሚልዮን ብር ባለይ በጀት አጸደቀ
መስራት እየቻሉ የገንዘብ እጥረት የገጠማቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን ችግሮች ለመፍታት የህብረት ስራ ማህበራት ሚና ቀላል አለመሆኑ ተገለጸ
በስልጤ ልማት ማህበር ለ3ኛ ጊዜ በተዘጋጀው የችግኝ ተከላ መርሀግብር ከሀገር ውስጥና ከውጪ ሀገር የተሰበሰቡ የአካባቢው ተወላጆች በዞኑ በሚገኙ የላንፉሮ ወረዳና ጦራ ከተማ አስተዳደር ችግኞችን ተክለዋል ።