በገቢ አሰባሰብ ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን ለመቅረፍና የ2017 እቅድ ለማሳካት ያለመ ውይይት እየተካሔደ ነው

ሀዋሳ፡ መስከረም 24/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በገቢ አሰባሰብ ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን በመቅረፍ በ2017 በጀት ዓመት ለመሰብሰብ የታቀደዉን 21 ቢሊዮን ብር ለማሳካት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከዞን መምሪያ ኃላፊዎች ጋር በአርባ ምንጭ ከተማ ዉይይት እያካሄደ ነዉ፡፡

ቢሮ “ተልዕኮዉን በብቃት የሚፈፅም ጠንካራና የፀና ተቋም መገንባት” በሚል መርህ ቃል የበጀት ዓመቱ 1ኛ ሩብ ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማና ክልላዊ ድጋፍና ክትትል ግብረ መልስ ዉይይት እያካሄደ መሆኑም ተመላክቷል፡፡

በዉይይት መድረኩ ላይ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የቢሮው ኃላፊ ወይዘሮ ዓለምነሽ ደመቀ በ2016 ዕቅድ አፈፃፀም ላይ የታዩ ውስንነቶች በ2017 እንዳይደገሙ የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር በተገኙበት ተገምግሞ ከስምምነት መድረሳቸዉን አንስተዋል፡፡

በበጀት ዓመቱ 21 ነጥብ 54 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ የታቀደዉን ዕቅድ ለማሳካት በክልሉ ያሉ ዞኖችን በ3 በማካፈል በኃላፊዎችና ከፍተኛ ባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል በማድረግ ሌሎችን በኮማንድ ፖስት በመከታተል የተሰበሰቡ መረጃዎችን መነሻ በማድረግ የታዩ ክፍተቶች ላይ ከመምሪያ ኃላፊዎች ጋር ዉይይት ማድረግ ማስፈለጉ ተመላክቷል፡፡

የክልሉን 75 በመቶ ወጪ ከዉስጥ ገቢ ለመሸፈን በክልሉ ም/ቤት በተቀመጠዉ አቅጣጫ መሠረት  ኢኮኖሚው የሚያመነጨው ሐብት ለመሰብሰብ የዞን መምሪያ ኃላፊዎችና ቢሮዉ በገቢ አሰባሰብ የፀና ተቋም በመፍጠር የሚወጡ አዋጆች፣ ደንቦችና መምሪያዎችን ተግባራዊ የማድረግ ኃላፊነት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ካታንሾ ካርሶ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን