ጤናው የተጠበቀና አምራች ዜጋን ለመፍጠር በጤናው ዘርፍ በየዓመቱ አዳዲስ የጤና አጠባበቅ ስልቶችን በመንደፍ ዘርፉን ማዘመን እንደሚያስፈልግ የደቡብ ኦሞ ዞን ጤና መምሪያ አስታወቀ

ይህ የተገለፀው የደቡብ ኦሞ ዞን ጤና መምሪያ የ2016 ዓ.ም ዕቅድ አፈፃፀምና የ2017 በጀት ዓመት የጤና መካከለኛ ዘመን ኢንቨስትመንት ዕቅድ ዙሪያ የሚመክር የባለድርሻ አካላት መድረክ በዲመካ ከተማ እየተካሄደ ባለበት ወቅት ነው።

በዞኑ 34 ጤና ጣቢያዎች፣ ከ172ቱ ጤና ኬላዎች 152ቱ ለህዝቡ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ፣ ሌሎቹ በተለያዩ ምክንያቶች አገልግሎት እንደማይሰጡ እና 3 አዳዲስ ጤና ጣቢያዎች በ2017 ዓ.ም ግንባታቸው እንደሚጠናቀቁ የደቡብ ኦም ዞን ጤና መምሪያ ሀላፊ አቶ ታምራት አሰፋ አብራርተዋል።

ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች ማህብረሰቡን መጠበቅና የግንዛቤ አሰጣጥ ሂደቱን ቀጣይነት ባለው መልኩ ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም ሀላፊው ጠቅሰዋል።

የዜጎች ጤና ተጠብቆ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጥ እንዲችሉ የሁሉንም አካል ልዩ ትኩረት ይሻል ሲሉም አቶ ታምራት አሳስበዋል።

የደቡብ ኦሞ ዞን የዋና አስተዳዳሪ ተወካይና የዞኑ ፐብሊክ ሰርቪስ መምሪያ ሀላፊ አቶ መልካሙ ሽበሺ ባስተላለፉት መልዕክት በ2016 ዓ.ም ከ11 ሺህ በላይ እናቶች በሰለጠነ ባለሙያ በጤና ተቋማት የወሊድ አገልግሎት ማግኘታቸውን ገልፀዋል።

መንግስት ሁሉም ዜጎች እኩል የጤና አገልግሎት ማግኘት እንዲችሉ እየሠራ መሆኑን ገልፀዋል።

በዚህም በዘርፉ ጉድለቶች እንዳሉ ሁሉ በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን አቶ መልካሙ ገልፀው ለማህበረሰቡ ግንዛቤ በመፍጠር የጤና አጠባበቁን በተሻለ መልኩ ማስቀጠል ያስፈልጋል ብለዋል።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን