የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ቢሮ የ2018 በጀት አመት የመጀመሪያ ግማሽ አመት አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በዱራሜ ከተማ እየተካሄደ ነው

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ቢሮ የ2018 በጀት አመት የመጀመሪያ ግማሽ አመት አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በዱራሜ ከተማ እየተካሄደ ነው

በመድረኩ ከቢሮው የግማሽ አመት አፈጻጸም በተጨማሪ የዲጂታል ክህሎት አተገባበርን በተመለከተ ውይይት እንደሚካሄድ ታውቋል።

በመድረኩ መክፈቻ ላይ የቢሮው ኃላፊ አቶ አሰፋ ደቼ ባደረጉት ንግግር፤ በቴክኒክና ሙያ ክህሎት ዘርፍ አዳዲስ ነገሮችን መማርና መላመድ ዘመኑ የሚጠይቀው ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል።

በሌላ በኩል ሙያው ራስን በኢኮኖሚ ለማበልጸግ የሚያስችል ድልድይ በመሆኑ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ ነው ብለዋል።

እንደ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተያዘው በጀት አመት 16 ሺህ 776 አዳዲስ ሰልጣኞችን ተቀብሎ ለማሰልጠን ቢታቀድም አፈጻጸሙ 65 በመቶ መሆኑን የቢሮ ኃላፊው አንስተዋል።

ነባር ሰልጣኞችን በተመለከተ በክልሉ ባሉ የስልጠና ተቋማትና ኮሌጆች ስልጠናውን እየተከታተሉ ከነበሩ ሰልጣኞች 93 በመቶ የሚሆኑት ስልጠናውን እየተከታተሉ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ለውጭ ሃገራት የስራ ስምሪት አጫጭር ስልጠናዎችን ለመስጠት ከታቀደው በላይ አፈጻጸም መመዝገቡን አቶ አሰፋ አስረድተዋል።

የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን ወደ ተጨባጭ ትግበራ ለማስገባት ወሳኝ እንደመሆናቸው ይህንን የማሳደግ ስራው በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በመድረኩ ኢትዮ ኮደርስን ወደ ተግባር ለመለወጥ ቁልፍ ሚና ያለው የዲጂታል ክህሎት አፈጻጸም መርሃ ግብርን በተመለከተ የውይይት መነሻ ጽሁፍ ቀርቦ ዉይይት ተካሂዶበታል።

በውይይት መድረኩ የሚመለከታቸው የስራ ኃላፊዎች የቴክኒክና ሙያ ትምህርት እና ስልጠና ተቋማት ኃላፊዎችና የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል።

ዘጋቢ: ወንድወሰን ሽመልስ