ህፃናትን በወቅቱ በማስከተብ ለተለያዩ በሽታዎች እንዳይጋለጡ እየተሰራ መሆኑን በቡርጂ ዞን ሶያማ ከተማ አስተዳደር ጤና ዩኒት ገለጸ
ከሚወለዱ ህፃናት አንድም ሳይከተብ እንዳይቀር በየቀበሌው ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታቋል።
በሶያማ ከተማ ጤና ጣቢያ ህፃናትን ሲያስከትቡ አግኝተን ካነጋገሪናቸው እናቶች መካከል ወ/ሮ ትዕግስት አወቀ፣ ወ/ሮ ኮሹ ደጀኔ እና ሌሎችም በሰጡት አስተያየት ከጤና ባለሙያዎች ባገኙት ግንዛቤ መሠረት ክትባቱን ሳያቋርጡ በወቅቱ አገልግሎቱ እየተሰጣቸው በመሆኑ ህፃናቱ ለተለያዩ በሽታዎች እንዳይጋለጡ እንደረዳቸው ተናግረዋል።
ክትባት ሲሰጡ ካገኘናቸው ባለሙያዎች መካከል የሶየማ ከተማ 01 ቀበሌ ጤና ኤክስቴሽን ባለሙያ ወ/ሮ ወርቅነሽ ማሞ ለህፃናት የሚሰጠው ክትባት የተለያዩ በሽታዎች እንደሚከላከል ጠቅሰው፥ ህፃናት በሽታ የመከላከል አቅማቸውን እንዲያሳድጉ ከመጀመሪያ ጀምረው ሳያቋርጡ መጨረስ እንደሚጠበቅባቸውም አስረድተዋል።
የሶያማ ከተማ አስተዳደር ጤና ዩኒት አስተባባሪ አቶ አየለ ሀይሶ በበኩላቸው በያዝነው በጀት ዓመት ባለፉት 6 ወራት 622 ህፃናት ለማስከተብ አቅደው በዘመቻ መልክ በመሥራት ወደ 743 ህፃናትን በማስከተብ ከዕቅድ በላይ ማሳካታቸውን አንስተዋል።
ዕቅዳቸው ግቡን የመታ ቢሆንም ከህፃናት ቁጥር አንፃር ብዙ መሥራት እንደሚጠበቅባቸው፣ ራቅ ያሉ ቀበሌያትም በከተማው ሥር በመታቀፋቸው የመንገድ ሁኔታ ምቹ ያለመሆንና የተሽከርካሪ እጥረት ተግዳሮቶች መሆናቸውን የጠቀሱት አስተባባሪው፥ ከህብረተሰቡ እና ከሌሎች ባለድረሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ችግሮቹን ለመፍታት እየሠሩ መሆናቸውን አብራርተዋል።
ዘጋቢ፡ ቦጋለ ሉሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን
ህፃናትን በወቅቱ በማስከተብ ለተለያዩ በሽታዎች እንዳይጋለጡ እየተሰራ መሆኑን በቡርጂ ዞን ሶያማ ከተማ አስተዳደር ጤና ዩኒት ገለጸ

More Stories
መጪው ጠቅላላ ምርጫ ተአማኒና በህዝቡ ዘንድ ቅቡልነት ያለው እንዲሆን በልዩ ትኩረት እንደሚሠራ የባስኬቶ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ደሣለኝ ገለፁ
የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት 4ኛ ዙር 28ኛ መደበኛ ጉባኤውን አካሂዷል
ለ7ኛ ጠቅላላ ምርጫ ዞናዊ የብልጽግና ፓርቲ ማኒፌስቶ እና የምርጫ መወዳደሪያ ምልክት የማስተዋወቂያ መርሐ ግብር በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ይገኛል