የታዳሽ ኃይል ማማ

በፈረኦን ደበበ

የኪንሻሳ ከተማ በውበት እንድትብረቀረቅ አድርጓታል፡፡ ዴሞክራቲክ ሪፑብሊክ ኮንጎ ከተጎናጸፈቻቸው በርካታ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች አንዱ ሲሆን የአፍሪካ ቀጣይ ተስፋ መሠረት እንደሆነም ተነግሮለታል፡፡

የቻይና ኩባኒያዎች ከሀገሪቱ መንግሥት ጋር በመተባበር የገነቡት ይህ ግዙፍ የኃይል ማመንጫ ግድብ በዋና ከተማዋ ኪንሻሳ የነበረውን ሥር የሰደደ ችግር እንደቀረፈም ተነግሯል በሚያመነጨው 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል፡፡

በሀገሪቱ ከተገነቡ 52 ያህል የኃይል ማመንጫዎች አንዱ የሆነው ይህ ግድብ በአስደናቂ ሁኔታ እንደተሠራና ኪንሻሳን ከሚያስፈልጋት ኃይል ከግማሽ በላይ ይሸፍናል፡፡ የሌሊት ሰማይዋንም በብርሃን አንዳንቆጠቆጠ የአፍሪካ ኒውስ ዘግቧል፡፡

በተለይ ቻይናዊያን ኃይል የሚገነቡ መሀንዲሶችና የኤሌክትሪክ ባለሙያዎች ከመድረሳቸው በፊት ከከተማዋ ዝቅተኛው ቦታ ውጭ ለሚኖሩት ሰዎች ሌሊቱ ከጨለማ እንደማይለይ የጠቆመው የዜና ምንጫችን፥ የ220 ኪሎ ቮልት ማስተላለፊያ መሥመሩ መጠናቀቅ ደግሞ ኃይልን ከዞንጋ ቁ.2 ወደ ማከፋፈያ ጣቢያዎቸ ለማሠራጨትም ረድቷል ብሏል፡፡

ኩንሳካ በተባለው ቦታ ወደ ሀገራዊ ቋት የሚቀላቀለው ይህ መሥመር ሱሳን የመሳሰሉ አካባቢ ነዋሪዎችን ሁሉ በደስታ እንዳስፈነጠዘ ጠቅሶ፥ በዕለት ተዕለት ህይወታቸው ላይም አወንታዊ ለውጥ አስገኝቷል ብሏል፡፡

የሱቅ ባለቤት የሆኑትን ማኗና ሚሲዮኖ ሮጀር የተባሉ ነዋሪን ያነሳው አፍሪካ ኒውስ፥ የህይወት ዘይቤያቸውን እንዳሻሻለላቸውና ሥራቸውን በአግባቡ ለማከናወን እንዳስቻላቸው ገልጿል፤ በፊት የነበሩባቸው ችግሮችን በመቅረፍ፡፡

በዋና ከተማይቱ የነበውን የኃይል አቅርቦት ችግር መቅረፉም በተለይ የሀገሪቱ ኤሌክትሪክ አቅራቢ ኩባኒያ አመራሮችን ሲያስደስት፥ በቀጣይም ከቻይና መሀንዲሶችና የኤሌክትሪክ ባለሙያዎች ጋር ትብብራቸውን ለማጠናከር በር ከፍቷል፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘ፥ የዞንጋ ቁ..2 ፕሮጀክት ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት ኪምቡማ አንገሊኮም በበኩላቸው ስለ ወደፊቱ ተስፋ ሲገልጹ፡- በሀገሪቱ ልማትን ለማምጣት የኤሌክትሪክ ኃይል አስፈላጊ መሆኑን ተናግረው በርካታ ቁጥር ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚረዳም አብራርተዋል፡፡

በቻይናዊያን የሚገነባው የኃይል ማመንጫ ለልማት ቁልፍ እንደሆነ ያስቀመጠው አፍሪካ ኒውስ፥ ለከተማዋም ሆነ ለሀገሪቱ ቀና መንገድ እንደሚፈጥር ገልጿል፡፡

ለአፍሪካም ሆነ ለዓለም የኤሌክትሪክ ኃይል ቀዳሚ ትኩረት በሆነበት በአሁኑ ጊዜ፥ ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው ሌላው ግድብ የቡሳንጋ ኃይል ማመንጫ ሲሆን በቻይናዊያን ገንዘብና የግንባታ ጥበብ የተከናወነም ነው፡፡

የሀገሪቱ ደቡብ ምሥራቃዊ ከተማ በሆነችው ሉዋላባ ላይ የተገነባው ይህ ፕሮጀክት ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው ባለፈው ዓመት ጥቅምት ወር ሲሆን ከሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ፈሊክስ ጸህሰኬዲም ከፍተኛ አድናቆት ማግኘት ችሏል፡፡

አካባቢውን የጎበኙት ፕሬዝዳንቱ የምረቃ ሪቫን ቆርጠው ሥራውን በይፋ ባስጀመሩበት ጊዜም የተለያዩ ክፍሎቹን ተዘዋውረው ተመልክተውታል፡፡ የሥራውን ዘመናዊነትና ጥራትም እንዳደነቁ የቻይና ዜና ማሠራጫ የሆነው ዥንዋ ዘግቧል፡፡

የውኃ ሀብትና የኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የሆኑት ኦሊቨር ሚዌንዜ ሙካለንግ በበኩላቸው፥ የኤሌክትሪክ አገልግሎትን ማስፋት የሀገራቸው ቀዳሚ ትኩረት መሆኑን አመልክተው፥ የቡሳንጋ ሀይድሮ ኤሌክትሪክ ማመንጫ የቻይናና ዴሞክራቲክ ሪፑብሊክ ኮንጎ ትብብር ውጤት ነው ብለዋል፤ የሀገራቸውን ዘመናዊነትና እንዲሁም አካባቢ ማህበረሰቡን እንደሚጠቅም በማስታወቅ።

በዴሞክራቲክ ሪፑብሊክ ኮንጎ የቻይና አምባሳደር የሆኑት፥ ዛኦ ቢንም ተመሳሳይ መልዕክት ነው ያስተላለፉት፤ በተለይ ብዙ የማዕድን ቁፋሮ ሥራዎች ለሚከናወኑበት ታላቁ የካታንጋ አካባቢ የሚሰጠውን ጠቀሜታ በማውሳት፡፡

ማዕድን ለሚቆፍሩ ኩባኒያዎች ኃይል ለማቅረብና የአካባቢ ነዋሪዎችን እንደሚጠቅም ገልጸው፥ ለዚህ የሚረዳ የላቀ ቴክኖሎጂ፣ ረጅም መወንጨፊያ ያላቸው መሣሪያዎች፣ የካበተ ልምድና የኢንቨስትመንት አቅም መኖሩንም ነው ያስታወቁት፤ ለሀገሪቱ ልማትና ብልጽግና አስተዋጽኦ መኖሩን ሁሉ በማመልከት፡፡

የቻይና ባቡር ኃይል አሰባሳቢ ቡድን እና የኃይል ግንባታ ኮርፖሬሽን የተባለው ኩባኒያ ከዴሞክራቲክ ኮንጎ መንግሥት ጋር በሽርክና ሠርቶታል የተባለለት የቡሳንጋ ውኃ ኃይል ማመንጫ 240 ሜጋ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም ሲኖረው፥ በዓመት እስከ 1 ነጥብ 32 ቢሊዮን ኪሎ ዋት ማመንጨት እንደሚችልም ነው የተጠቆመው፡፡

ከላይ ከተገለጹት ፕሮጀክቶች በተጨማሪ እስከ 50 የሚደርሱ ሌሎች ግድቦች አሏት ተብላ የምትታወቀው ሀገር፥ በእርግጥ የአህጉሪቱ የውኃ ኃይል ማማ ተብላ መገለጽ ትችላለች፤ ከደቡብ አፍሪካ ጀምሮ በርካታ ሀገራት የሚገነቡትን ታላቁ የእንጋ ll የኃይል ማመንጫ ሁሉ ደግፋ ስለያዘች፡፡

ይሁን እንጂ፤ እየመነጨ ያለው ኃይል አህጉሪቱ ከምትፈልገው ሩብ እንኳን ያለመሸፈኑ ያሳዝናል፤ ምክንያቱም ብዙ ሀገራት እስካሁን በችግር ውስጥ ስለሚገኙ፡፡ በተለይ እንደ ኬኒያ፣ ናይጀሪያና ደቡብ አፍሪካ በመሳሰሉ ታላላቅ ሀገራት እየተስተዋለ ያለው ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ቀውስ አሳሳቢ ስለሆነ፡፡

የዴሞክራቲክ ሪፑብሊክ ኮንጎ ውስጣዊ የጸጥታ ሁኔታዎችም እንዲሁ ያሉበት ደረጃ ያሳስባል ፤ ምክንያቱም በምሥራቃዊ ግዛቷ ባለው ቀውስ እንደ ሩዋንዳ ያሉ ጎረቤት ሀገራት እጅ ሁሉ አለበት ተብሎ ስለሚታሰብ።

ሀገሪቱ ከውኃ ባለፈ በማዕድን ሀብትም የበለጸገች ሲሆን ይህ ግጭት ከማባባስ ባለፈ ትሩፋት ማስገኘት ያለመቻሉ ያስቆጫል። ምንም እንኳን የቻይና ኩባኒያዎች የሚፈጥሩት ዕድል ለዘላቂ ልማት ትልቅ አስተዋጽኦ ቢኖረውም፡፡

የአፍሪካ ህብረትና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትም ቢሆን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ላለባቸው አካባቢዎች ተገቢ ትኩረት አድርገው ቢሠሩ አፍሪካዊያንን ከሚገኙበት የድህነት አዙሪት ለማውጣት ይረዳል፡፡