“መስማት የተሳነኝ መሆኔ ከመማርና ዓላማዬን ከማሳካት አላገደኝም” – አቶ ዮሐንስ ተክላይ

በመሐሪ አድነው

አቶ ዮሐንስ ተክላይ ተወልዶ ያደገው በትግራይ ክልል አክሱም ከተማ ነው፡፡ የሠባት አመት ልጅ እያለ በአካባቢው ተከስቶ በነበረ የማጅራት ገትር በሽታ ተይዞ መስማትም መናገርም ተሳነው፡፡

አቶ ዮሐንስ እንደሚለው የሁለተኛ ክፍል ተማሪ በነበረበት ጊዜ ነበር ይህ የአካል ጉዳት የደረሰበት፡፡ በዚያን ወቅት እርሱ በተወለደበት አካባቢ መስማትና መናገር የተሳነው ሠው አይቶ የማያውቅ በመሆኑ ለህክምና ሲወሰድ በአለም ላይ ብቸኛው ተጠቂ እንደሆነ ሲነገረው ተስፋ ቆርጦ ነበር፡፡ ምክንያቱም የአካል ጉዳት ሳይደስበት በፊት የነበረው ማህበሪዊ ግንኙነት በአንድ ጊዜ በመቋረጡ ነበር ይህ ስሜት የተፈጠረበት፡፡

እንደዚያም ሆኖ ትምህርቱን መስማትና መናገር ከሚችሉት ጋር አብሮ ነው የቀጠለው፡፡ ነገር ግን ወደ ክፍል መግባት መውጣት ብቻ እንጂ መምህራኑ የሚሉትን ነገር የሚረዳበት አጋጣሚ የለውም፡፡ አስተማሪው የፃፈውን ብቻ መገልበጥ ነው፡ ፡ ይህችንም ታህል የረዳው አስቀድሞ ፊደል ቁጠር መቻሉ ነው፡፡

በዚህ መልኩ እየተፍጨረጨረ 8ኛ ክፍል ደረሰ፡፡ እስከ 6ኛ ክፍል ድረስ እንግሊዝኛ መፃፍና ማንበብ አይችልም ነበር፡፡ ከ8ኛ ክፍል በኋላ ደግሞ አብዛኛው ትምህርት የሚሰጠው በእንግሊዝኛ በመሆኑ ተስፋ ቆርጦ ትምህርቱን ለማቋረጥ ወስኖ ነበር፡፡ ነገር ግን አጐቱ ተስፋ እየሰጠውና እያበረታታው ወደፊት ወደ ውጭ ሃገር መሄድ እንደሚችል እየነገረው ትምህርቱን እንዲቀጥል አደረገው፡፡ የጓደኞቹም ማበረታታት ተስፋው እንደገና እንዲለመልም አድርጐታል፡፡ በዚህ ሁኔታ ትምህርቱን ቀጥሎ ዘጠኝ እና አሥርን ከጨረሰ በኋላ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ቻለ፡፡

በዚህም አዲስ አበባ ኮተቤ መምህራን ማሰልጠኛ ኮሌጅ መግባቱንና አሁንም ተግዳሮቱ እንደቀጠለ ነው የገለፀው፡፡ በኮሌጁ የሚማሩት ሁሉ መስማት የሚችሉ ናቸው ከእርሱ በቀር፡፡

ይሁን እንጂ ኮሌጅ እስከገባበት ጊዜ ድረስ የነበሩትን ተግዳሮቶች ተቋቁሞ በድል እዚህ መድረሱ ፅናትን ያጎናፀፈው በመሆኑ ራሱን በድጋሚ አጀግኖ ትምህርቱን ለመቀጠል ወሰነ፡፡ በተፈጥሮ ሳይንስ ትምህርት በከፍተኛ ማዕረግ ለመመረቅም በቃ፡፡

በዚህ ውጤት ሞራሉ የተነቃቃው አቶ ዮሐንስ በኢትዮጵያ የምልክት ቋንቋ ጥናት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለሁለተኛ ጊዜ በማአረግ መመረቅ ችሏል፡፡

ሁለተኛ ዲግሪውን ደግሞ በልዩ ፍላጐት ትምህርት አሁንም በከፍተኛ ውጤት ተመርቋል፡፡ በትምህርት የነበረውን ቆይታ በርካታ ችግሮችንና ተግዳሮቶችን ተሻግሮ ዛሬ ላይ ውጤታማ ለመሆን በመቻሉ ኩራት ይሰማዋል፡፡

መስማት የተሳነኝ መሆኔ ከመማርና ዓላማዬ ከማሳካት አላገደኝም፡፡ ዋናው የራስን ፅናት ነው የሚጠይቀው ይላሉ አቶ ዩሐንስ ተክላይ፡፡

ወደ ሥራው ዓለም ከገቡበት ጊዜ ጀምሮም በተለያዩ ተቋማት መስራት ችለዋል፡፡ በምህፃሩ DDIA (Deaf De­velopment Information Associa­tion) በሚባል ተቋም በአካቶ ትምህርት የኘሮጀክት አስተባባሪ በመሆን ሠርቷል፡፡

በስምንት የተለያዩ ት/ቤቶችና በአራት ክልሎች ማለትም ደቡብ ፣ አማራ፣ ትግራይና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ላይ ነው ለ4 አመታት ሲሰራ ቆይቷል፡፡

አሁን ላይ ደግሞ በኢትዮጵያ አካል ጉዳተኛ ልማት ማእከል በምህፃሩ ECDD (Ethiopia Center for Disability De­velopment) በተሠኘ ተቋም ውስጥ በአካቶ ትምህርት ኘሮጀክት አስተባባሪ ሆኖ እየሠራ ይገኛል፡፡

ተቋሙ በዋናነት የሚሠራው በከፍተኛ የትምህርት ተቀማት ውስጥ ባሉ አካል ጉዳተኛ ተማሪዎች ላይ የአቅም ግንባታ ሥራ ላይ ነው ትኩረት የሚያደርገው፡፡ ሥራ የሚሠራባቸው ዩኒቨርሲቲዎች ባህር ዳር፣ ጂጂጋ እና ወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲዎች ናቸው፡፡

ከዚህም በተጨማሪ አቶ ዮሐንስ ተክላይ የኢትዮጵያ መስማት የተሳናቸው ስፖርቶች ፌዴሬሽን ኘሬዝዳንትም ነው፡፡ በዚህም መስማት የተሳናቸው ዜጐች በተለያዩ ስፖርቶች ላይ እንዲሳተፉ እያበረታታ እንደሚገኝም ገልጿል፡፡ በቅርቡ በተደረገው ምርጫ ደግሞ የኢትዮጵያ መስማት የተሳናቸው ብሄራዊ ማህበራት ኘሬዝዳንት በመሆን ተመርጦ እያገለገለ ይገኛል፡፡

አቶ ዮሐንስ የአፍ መፍቻ ቋንቋው ትግርኛ በመሆኑ እንግሊዝኛን ብቻ ሳይሆን የአማርኛ ቋንቋም አይችል ነበር፡፡ ነገር ግን ሁሉም ነገር በራስ ጥረት እንደሚገኝ የሚያምን መንፈስ ብርቱ ስለነበር አሁን ላይ ሁለቱንም ቋንቋ ጥርት አድርጐ ይናገራል ይፅፋል፡፡ የማትሪክ ውጤቱም በሁለቱም የትምህርት አይነት A ነው ያመጣው፡፡

ሁላችንም የአማርኛውንም ሆነ የእንግሊዝኛውን ፊደል ቆጥረን ነው ትምህርት የጀመርነው፡፡ ነገር ግን ፍላጐት ከጨመርንበት የማንደርሰው ቦታ የለም የሚሉት አቶ ዮሐንስ ለሁሉም ስኬት የራስ ጥረት ያስፈልጋል ባይ ናቸው፡፡

መስማት የተሳናቸው ሠዎች ከፍተኛው ችግራችን ከሌሎች ዜጐች እኩል መረጃ ማግኘት አለመቻላችን ነው፡፡ በምህፃሩ CRPD የተሠኘው ዓለም አቀፍ ተቋም እኛም መረጃ የማግኘት መብት እንዳለን አስቀምጦልናል፡፡ ከዚያም ባለፈ ሠው በመሆናችን ብቻ መረጃ የማግኘት መብት አለን፡፡

ወደ 5 ሚሊዮን የሚቆጠሩ መስማት የተሳናቸው ዜጐች በኢትዮጵያ ውስጥ እንዳሉ ይነገራል፡፡ ይህን ያህል ማህበረሰብ መረጃ አይሠጠውም ማለት ያላቸውን አበርክቶ ካለማጤን የመጣ ነው፡፡ ከዚህም በላይ በሀገሪቱ ላይ የሚያሳድረው ተፅእኖም ከባድ በመሆኑ ለእነርሱ መረጃ አለመስጠት አግባብ አይደለም ዋጋም ያስከፍላል የሚል እምነት ነው አቶ ዮሐንስ ያለው፡፡

በሬዲዮ የሚተላለፉ መረጃዎች መስማት ለተሳናቸው ወገኖች ተደራሽ አይደሉም፡፡ የቴሌቪዥን ጣቢያዎቻችንም እምብዛም አስተርጓሚ ያላቸው አይደሉም።

አልፎ አልፎ ከሚከሰቱ ኩነቶች በስተቀር። መስማት የተሳናቸው የቴሌቪዥን ኘሮግራምም ቢሆን በሳምንት አንድ ቀን ብቻ ነው ያለው ይህም በቂ አይደለም፡፡

እንደ ዜጋ አስተርጓሚ የማግኘት መብታችን በአንዳንድ መድረኮች ላይ በእንግድነት ብንጋበዝም ኘሮቶኮሉ አይፈቅድም በሚል ሠበብ ከፊት ለፊት እንድንቀመጥና በአስተርጓሚ እንድንሰማ አይደረግም ሲል በአፅንኦት ገልጿል፡፡ ይሄ ደግሞ መረጃ የማግኘት መብታችንን መጣስ ነውና መታረም አለበት ይላል፡፡

በሀገራችን ጉዳይ እኛም ሃሳብ የማዋጣት የዜግነት መብታችን ሊከበር ይገባል ሲል አቶ ዮሐንስ ተክላይ ጠቁሟል፡፡