በህብረተሰብ ተሳትፎ እየተሰራ ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት ስራ አበረታች መሆኑን በዳውሮ ዞን የኢሠራ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ

በህብረተሰብ ተሳትፎ እየተሰራ ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት ስራ አበረታች መሆኑን በዳውሮ ዞን የኢሠራ ወረዳ አስተዳደር አስታወቀ

ሀዋሳ፡ የካቲት 26/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) በህብረተሰብ ተሳትፎ እየተሰራ ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት ስራ አበረታች መሆኑን በዳውሮ ዞን የኢሠራ ወረዳ አስተዳደር አስታውቋል፡፡

ህብረተሰቡን ያሳተፈ የመንገድ መሰረተ ልማት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው የተጠቆመው፡፡

የኢሠራ ወረዳ በውስጡ 29 ቀበሌያትን የያዘ ሰፊ ወረዳ ነው። ይሁን እንጂ ግን በወረዳው   ቀበሌን ከቀበሌና ከወረዳ ማዕከል ጋር የሚያገናኝ የመንገድ መሰረተ ልማት ተደራሽ ባለመሆኑ ምክንያት ህብረተሰቡም በዚሁ ምክንያት ሲቸገሩር ነው የቆዩት።

የኢሠራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሰለሞን ተክሌ፤ ከጉዳዩ ጋር ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ ይህንኑ ነው ያረጋገጡት። ችግሩ እንዳይፈታም በወረዳው ያለው የበጀትና የአቅም ውስንነት አግዷቸው እንደቆየ በመግለጽ።

የወረዳው መንግስት እንደ መንግስት ችግሩን ለማቃለል የአማራጭ መፍትሔ መንገዶችን ሲያፈላልግ መቆየቱን ያወሱት ዋና አስተዳዳሪው የወረዳ መንግስት ብቻውን የመንገድ ተደራሽቱን ችግር ለመፍታታ የበጀትና አቅም ውስንነት ያለበት በመሆኑ የህብረተሰብ ተነሳሽነት ከጉዳዩ ጋር መታከል ስላለበት ለህብረተሰቡ ግንዛቤን የመፍጠሩ ስራ በስፋት ሲሰራበት እንደነበረ አስረድተዋል።

ይህን ተከትሎ በተፈጠረው ግንዛቤም መሰረት በሁሉም ቀበሌያት የሚገኙ የወረዳው ህብረተሰብ ክፍሎች አሁን ችግሩን ለመፍታት መንግስትን ሳይጠብቁ በራሳቸው ተነሳሽነት በየአከባቢያቸው የመንገድ ስራን እየሰሩ ይገኛሉ ብለዋል ዋና አስተዳዳሪው።

የመንግስት ጥሪን በመቀበል ህብረተሰቡ አሁን እያሳየ ያለው ተነሳሽነት የሚበረታታ እንደሆነ የገለፁት አቶ ሰለሞን ለስራው ስኬታማነት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ላበረከቱት ሁሉም ምስጋና አቅርበዋል።

በህብረተሰቡ ተሳትፎ እየተሰሩ ያሉ መንገዶች ዘላቂ አገልግሎት እንዲሰጡ ለማስቻልም የወረዳው መንግስት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት ቀጣይ ጠጠር ለማልበስ እቅድ መያዙንም አስረድተዋል።

የኢሠራ ወረዳ መንገድና ትራንስፖርት ልማት ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ አያልቅበት አስፋው በበኩላቸው በወረዳው ሰፊ የሆነ የመንገድ ተደራሽነት ችግር  ያሉት መሆኑን  አንስተው አሁን ቀበሌን ከቀበሌና ከወረዳ ማዕከል ጋር የሚያገናኝ የአዲስ መንገድ ከፈታና የጥገና ስራ በትኩረት እየተሰራበት እንዳለ ገልፀዋል።

በዚህም በዱዚ ማዘጋጃ ከተማ ውስጥ ለውስጥ የ15 ኪሎ ሜትር መንገድ ከፈታና ከዱዚ ማዳ ዋሳራ እስከ ደንጋ ቀበሌ ድረስ የ27 ኪሎ ሜትር የማስፋፊያ ስራ በህብረተሰቡ ተሳትፎ የተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

በአከባቢው አግኝተን ካነጋገርናቸው ነዋሪዎች መካከል አቶ ተስፋዬ መንገሻ፣ አቶ ቡቴ ባካሌ እና አቶ ፋላ ካረታም በአካባቢያቸው የመንገድ መሰረተ ልማት ተደራሽ ባለመሆኑ ምክንያት ሲቸገሩ መቆየታቸውን በመግለፅ አሁን ላይ ከመንግስት ጎን በመቆም የበኩላቸውን ሚና በመወጣት ላይ መሆናቸውንና ስራው እስኪጠናቀቅ ድረስ ድጋፋቸውን እንደሚቀጥሉ ገልፀዋል።

ዘጋቢ፡ አማኑኤል ተገኝ – ከዋካ ጣቢያችን