የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት በጂንካ ከተማ መስጠት ተጀመረ

የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት በጂንካ ከተማ መስጠት ተጀመረ

ሀዋሳ፤ የካቲት 25/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ጤና ቢሮ ከአሪ ዞን ጤና መምሪያ ጋር በመተባበር ዕድሜያቸው 14 ዓመት ለሞላቸው ሴቶች የመማፀን በር ጫፍ ካንሰር መከላከያ ክትባት በጂንካ ከተማ መስጠት ጀምሯል፡፡

ክትባቱ ከየካቲት 25 እስከ 29 ቀን 2016ዓ.ም በክልሉ ሁሉም ዞኖች እንደሚሰጥ ተገልጿል።

በክትባት ማስጀመሪያ መርሀግብር ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብረሃም አታ ባለፉት 6 ወራት በዞኑ ለ60 ሴቶች የማህፀን በር ጫፍ ካንሰር ክትባት መሰጠቱን ገልጸው በ20 ሴቶች ላይ በሽታው እንደተገኘ ተናግረዋል፡፡

እየተሰጠ ያለው ክትባት ተመሳሳይ ችግር እንዳይከሰት እንደሚረዳ አረጋግጠዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ እንደሻው ሽብሩ የማህፀን በር ካንሰር ክትባት የበሽታውን ስርጭት 90 በመቶ ለመከላከል እንደሚረዳ ገልፀዋል።

በክልሉ በሚገኙ ሁሉም አከባቢዎች በቀጣይ 5 ቀናት በሚሰጠው ክትባት 154ሺ 848 ሴቶች ይከተባሉ ብለዋል፡፡

አስፈላጊው ግበዓትና የሰው ኃይልም በሁሉም አካባቢዎች ተሰማርቷል፡፡

የጤና ሚኒስቴር ተወካይ አቶ ሠለሞን ዘለቀ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ከሚያከናውናቸው ተግባራት አንዱ የማህፀን በር ካንሰር ክትባት አንዱ መሆኑን አመላክተው በተያዘው የክትባት ዘመቻ በሀገር አቀፍ ደረጃ 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን የሚሆኑ ልጃገረዶች ክትባቱን ያገኛሉ ብለዋል፡፡

ለክትባቱ ስከታማነት ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ኃላፊነቱን እንዲወጡ አቶ ሠለሞን ጥሪ አቅርበዋል።

ዘጋቢ፡- መልካሙ ቡርዝዳቦ- ከጂንካ ቅርንጫፍ