በክብር እንግድነት ኢትዮጵያ የደረሰው ባካሪ ሳኛ

በክብር እንግድነት ኢትዮጵያ የደረሰው ባካሪ ሳኛ

የቀድሞ የአርሰናል እና የፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድን የመስመር ተከላካይ ባካሪ ሳኛ በዛሬው ዕለት ኢትዮጵያ ገብቷል።

ባካሪ ሳኛ በመጪው ማክሰኞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ይፋዊ የትጥቅ አቅራቢ ማክሮን በሚያበስረው መርሐግብር ላይ በክብር እንግድነት ለመታደም አዲስ አበባ መድረሱን ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

የ42 ዓመቱ ባካሪ ሳኛ ወደ አዲስ አበባ ሲደርስ የፌዴሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ባህሩ ጥላሁን በቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በመገኘት አቀባበል ማድረጋቸው ተገልጿል።

እንደ አውሮፓውያኑ በ2017 ለመጨረሻ ጊዜ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የተጫወተው ሳኛ ለአርሰናል ማንቸስተር ሲቲ ከ260 በላይ የፕሪሚዬር ሊግ ጨዋታዎችን አከናውኗል።

ለፈረንሣይ ብሔራዊ ቡድን ደግሞ በ65 ጨዋታዎች ተሰልፎ ተጫውቷል።

ባካሪ ሳኛ በአሁኑ ሰዓት በዩናይትድ አረብ ኤምሬት የሚገኘውን ባናት የሴቶች እግርኳስ ክለብን በዋና አሰልጣኝነት እየመራ ነው።

ዘጋቢ፡ሙሉቀን ባሳ