የጤና አገልግሎት ተደራሽነትና ጥራትን ለማረጋገጥ በዘርፉ ለሚታቀዱ  ዕቅዶች ተግባራዊነት ልዩ ትኩረት ሊሰጣቸው  እንደሚገባ ተገለጸ

የጤና አገልግሎት ተደራሽነትና ጥራትን ለማረጋገጥ በዘርፉ ለሚታቀዱ  ዕቅዶች ተግባራዊነት ልዩ ትኩረት ሊሰጣቸው  እንደሚገባ ተገለጸ

ሀዋሳ፤ የካቲት 23/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) የጤና አገልግሎት ተደራሽነትና ጥራትን ለማረጋገጥ በዘርፉ ለሚታቀዱ  ዕቅዶች ተግባራዊነት ልዩ ትኩረት ሊሰጣቸው  እንደሚገባ ተገለጸ።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ጤና ቢሮ የጤናው ዘርፍ መካከለኛ ዘመን ልማትና ኢንቨስትመንት ዕቅድ ማስጀመሪያ ዙሪያ ለባለድርሻ አካላት ስልጠና ሰጥቷል።

ዕቅዱ ለሚቀጥሉት ተከታታይ 3 አመታት በሁሉም የጤና ማዕቀፎች ተግባራዊ የሚደረግ መሆኑም ተመላክቷል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ እንደሻው ሽብሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት  የጤናው ዘርፍ መካከለኛ ዘመን ልማትና ኢንቨስትመንት ዕቅዱ ለዘርፉ ስኬት የጀርባ አጥንት በመሆኑ ለተፈፃሚነቱ የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።

ዝርዝር የዕቅዱን ይዘት ለታዳሚው ያቀረቡት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ጤና ቢሮ የጤና ልማት ዕቅድና ኢኮኖሚ አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ተገኝ ጮቴ በበኩላቸው የጤናው ዘርፍ መካከለኛ ዘመን ልማትና ኢንቨስትመንት ዕቅዱ ከ2016-2018 ዓ.ም የተግበር መሆኑን አብራርተዋል።

ዕቅዱ  የጤናውን ዘርፍ እቅድ ከሀገሪቱ አጠቃላይ ፕላንና ዕቅድ ጋር አጣጥሞ ለመተግበር የተያዘውን የመንግስት አቅጣጫ መሠረት ያደረገ ነው ብለዋል።

የቀረበው የጤናው ዘርፍ ልማትና ኢንቨስትመንት ዕቅድ የማስፈፀሚያ ስልቶችን ጨምሮ በየአካባቢዉ ያለዉን ነባራዊ ሁኔታ ታሳቢ ያደረገ  በመሆኑ በቀጣይ የልማት ግቡን ለማረጋገጥ የሚረዳ ነው  ሲሉ ከተለያዩ ዞኖች የመጡ የስልጠናው  ተሳታፊዎች ገልጸዋል።

የማይበገር የጤና ስርዓትን መገንባትን የዕቅዱ ሚና የላቀ ስፍራ ይሰጠዋል፤ በዚህም ስኬት ህብረተሰብን በባለቤትነት የማሳተፍ፣ የፋይናንስ፣ የግንባታ እንዲሁም የጤና ተቋማት ግንባታ ጉዳይ በዕቅዱ መካተት እንደሚገባቸው አንስተዋል።

ተግባራትን በእቅድ ደረጃ ከማውረድ በዘለለ ተፈጻሚነታቸውን በየጊዜው መከታተል ሌላኛው የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን የቢሮው ምክትል ኃላፊና የህክምና አገልግሎቶች ዘርፍ ኋላፊ አቶ ናፍቆት ብርሀኑ በሰጡት ማብራሪያ ገልጸዋል።

ዘጋቢ: አወል ከድር – ከሳውላ ጣቢያችን