የወጪ ምርቶችን ድርሻ በማሳደግ 1 ነጥብ 53 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ማግኘት ተችሏል

የወጪ ምርቶችን ድርሻ በማሳደግ 1 ነጥብ 53 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ማግኘት ተችሏል

ሀዋሳ፡ የካቲት 06/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) ዋና ዋና የወጪ ምርቶችን ድርሻ በማሳደግ 1 ነጥብ 53 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ።

ህገወጥ የንግድ ስርአቱን መከታተልና መቆጣጠር እንደሚገባም ተነስቷል።

ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የ6 ወር እቅድ አፈጻጸሙን በገመገመበት ወቅት የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ገብረ መስቀል ጫላ እንደገለጹት ባለፈው ግማሽ አመት በሀገር አቀፍ ደረጃ 1 ሚሊየን 381 ሺህ 938 የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አገልግሎት በኦንላይን መሠጠቱን ተናግረዋል።

አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ የሚያገናኙ የቅዳሜና እሁድ የገበያ ማእከላትን በማስፋፋት ቁጥሩን ወደ 855 ከፍ ያለ ሲሆን በገበያው የተለያዩ የኢንዱስትሪና ግብርና ምርቶች ቀርበው ግብይት እየተካሄደባቸው ነው ብለዋል።

የዋና ዋና ወጪ ምርቶችን ድርሻ ከማሳደግ ረገድ 1ቢሊየን 527 ሚሊየን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን የገለጹት ሚኒስትሩ ገቢው ከባለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ 12 ነጥብ 88 ከመቶ ቅናሽ ማሳየቱን ገልጸው በቀሪ ወራት በተሳካ መልኩ ለመስራት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

ከቅባት እህሎች ከጥራጥሬ ከጫት ምርትና ከመሠል ምርቶች 402 ሺ 71 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ መገኘቱንና ይህም ከአምናው ጋር ሲነጻጸር 30 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን ጠቅሰዋል።

በአጠቃላይ ዋና ዋና የወጪ ምርቶችን ድርሻ በማሳደግ 1 ቢሊየን 527 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉንም ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

ዘጋቢ ፡ ማርታ ሙሉጌታ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን