ዘመናዊ የመሬት ሕግ ሥርዓት መዘርጋትና ተቋማዊ አቅምን መገንባት ለሀገር ዕድገት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ
ሀዋሳ፡ መጋቢት 06/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ዘመናዊ የመሬት ሕግ ሥርዓት መዘርጋትና ተቋማዊ አቅምን መገንባት ለሀገር ዕድገት ወሳኝ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መሬት አስተዳደር ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር እና ከጀርመን ዓለም አቀፍ ትብብር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የሕግ ማዕቀፍ ግብዓት ማሰባሰቢያ መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።
በግብርና ሚኒስቴር የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ትዕግስቱ ገብረመስቀል፥ የመሬት አስተዳደር ጉዳይ ልዩ ትኩረትና ድጋፍ የሚሻ የልማት ዘርፍ መሆኑን ገልጸዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መሬት አስተዳደር ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዶ/ር ዮሴፍ ማሩ በበኩላቸው፥ የመሬትን ፋይዳ ያገናዘበ የሕግ ማዕቀፍና አደረጃጀት ማስፈለጉን ተናግረዋል።
በGIZ ኢትዮጵያ የመሬት አስተዳደር ፕሮጀክት የፖሊሲና የሕግ አማካሪ ዶ/ር ዳንኤል በኃይሉ በበኩላቸው፤ ግልጽ ሕግ እንዲሁም የማስፈፀም አቅም ያለው አደረጃጀትና የሰው ኃይል መኖሩ በማህበረሰቡ ውስጥ የሚስተዋሉ በርካታ ችግሮችን እንደሚፈታ ገልጸዋል።
የሕግ ማዕቀፍ ሰነዱን ካቀረቡት ባለሙያዎች መካከል በክልሉ የመሬት አስተዳደር ይዞታ አስተዳደር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ጳውሎስ ባርጉዴ እንደገለጹት፥ የክልሉ መሬት አስተዳደር ቢሮ እንደ አዲስ መዋቀሩን ተከትሎ አዲስ የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኗል።
በውይይቱ ላይ የተሳተፉ ባለድርሻ አካላትም የሚወጡ ሕጎችን ከሌሎች ነባር ሕጎች ጋር እንዲናበቡ መደረግ እንዳለበት ጠቁመው፥ መካተት በሚገባቸው ነጥቦች ላይ አስተያየቶች ተሰጥቷል።
ዘጋቢ: አማሮ አርሳባ – ከአርባ ምንጭ ጣቢያችን

More Stories
ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኮረሪማ ምርት እየለማ መሆኑ ተገለጸ
በጎፋ ዞን ከ12 ሺህ በላይ ተማሪዎች ክልላዊ የ6ኛ ክፍል ፈተና እየተሰጠ ነው
የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች በመመለስ በኩል ከመንግስት ጥረት ባለፈ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሚና የጎላ መሆኑን የደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተመስገን ከበደ ተናገሩ