የበለፀገ ማህበረሰብ በመፍጠርና ዘላቂ ልማትን እውን በማድረግ የኢትዮጵያን ብልጽግና ለማረጋገጥ ሲቪል ሰርቫንቱ የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተጠቆመ

የበለፀገ ማህበረሰብ በመፍጠርና ዘላቂ ልማትን እውን በማድረግ የኢትዮጵያን ብልጽግና ለማረጋገጥ ሲቪል ሰርቫንቱ የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ ተጠቆመ

“አገልጋይ፣ ስልጡንና ስብጥር ሲቪል ሰርቫንትን መፍጠር” በሚል መርህ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአሪ ዞን ማዕከል ሲቪል ሰርቫንት የአቅም ግንባታ ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል።

ስልጠናው ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚሰጥ ሲሆን በደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ጂንካ ቅርንጫፍ አዳራሽ የተቋሙ ሠራተኞችን ጨምሮ የዞኑ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ፣ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት መምሪያና ሳይንስና ቴክኖሎጂ መምሪያ ሠራተኞች ተሣትፈዋል።

ስልጠናውን በንግግር የከፈቱት የአሪ ዞን ብልጽግና ፖርቲ ጽ/ቤት ፖለቲካ ዘርፍና የዞኑ መንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ግዛቸው በላይ እንደገለፁት ለ6 ዙር እየተሰጠ ያለው ስልጠና አጠቃላይ የሲቪል ሰርቫንቱን የመፈፀም አቅም በመገንባት ራሱንና ሀገሩን ወደ ብልጽግና እንዲያሸጋግር ለማስቻል ያለመ ነው።

እንደ ሀገር እየተባባሰ የመጣውን የኑሮ ውድነትና ዋጋ ንረትን ለማስቀረት ስራ ፈቱን ወደስራ ማስገባትና ለሥራ አጡ ደግሞ ስራን በመፍጠር በአጠቃላይ ሲቪል ሰርቫንቱ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ በመድረኩ ተገልጿል።

ከስልጠናው ተሣታፊዎች መካከል ወ/ሮ ልቯቯ ፋንታውና ዘውዲቱ ፀጋዬ ስልጠናው ያላቸውን ተፈጥሯዊና ሙያዊ ፀጋዎቻቸውን ተጠቅመው እንዴት ሀብት መፍጠር እንዳለባቸው የሚያነሳሳና ዕውቀት የቀሰሙበት መሆኑን ጠቁመው በቀጣይ በስልጠናው ያገኙትን ዕውቀት በራሳቸው ሕይወትና ሌሎችን ለማሳተፍ ዝግጁ መሆናቸውን ገልፀዋል።

ስልጠናው በዞኑ ማዕከል ጂንካ ከተማ በተለያዩ ቡድን ተከፋፍሎ እየተሰጠ ይገኛል።

ዘጋቢ፡ ተመስገን ሠይፉ – ከጂንካ ጣቢያችን