የፍትህ ስርዓቱን ተደራሽና ቀልጣፋ ለማድረግ እየተሰራ ነዉ – የካፋ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት

ሀዋሳ፡ የካቲት 25/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የፍትህ ስርዓቱን ተደራሽና ቀልጣፋ ለማድረግ የባህልና መደበኛ ፍርድ ቤቶችን አቀናጅቶ እየሰራ መሆኑን የካፋ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት አስታወቀ።

የዞኑ ፍርድ ቤቶች የግማሽ አመት አፈጻጸም ግምገማና የመልካም አስተዳደር መድረክ መካሄድ ጀምሯል።

የፍርድ ቤቱ ፕሬዝዳንት አቶ መንግስቱ ከበደ በመድረኩ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፥ በየደረጃው የሚገኙ ፍርድ ቤቶች መልካም አስተዳደርንና ፍትህን ለማስፈን የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወኑ ይገኛል ብለዋል።

የቀበሌ ማህበራዊ ፍርድ ቤቶችና ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ለፍትህ ተደራሽነት እያበረከቱ ያሉት አስተዋጽዖ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመዋል።

መልካም አስተዳደርን ለማስፈን በየደረጃው በሚገኙ አፈ-ጉባኤዎች የህዝብ አስተያየት የመሰብሰብና ለፍርድ ቤቶች መረጃ የመስጠት ስራ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል።

በበጀት አመቱ በወንጀልና ፍታብሔር 11 ሺህ 364 መዝገቦች ቀርበው 9 ሺህ 948 መዝገቦች ላይ ውሳኔ መሰጠቱን ገልጸዋል።

የቀሩት 1 ሺህ 416 መዝገቦች ለቀጣይ በጀት አመት መተላለፋቸውን የገለጹት ፕሬዝዳንቱ አፈጻሙ 87 በመቶ በላይ መሆኑንም ገልጸዋል።

በመድረኩ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ጥላሁን ታደመ፣ የካፋ ዞን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ወ/ሮ አሚናት ሀሰንን ጨምሮ የወረዳና ከተማ አስተዳደሮች ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንቶችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነዉ።

ዘጋቢ፡ ባርታ ታዬ – ከቦንጋ ጣቢያችን