7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬታማ እንዲሆን ሴቶች በግንባር ቀደምነት በመሳተፍ የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተገለጸ

‎ምርጫው ነፃ፣ ሰላማዊ፣ ፍትሀዊና ተአማኒነት ያለው ሆኖ እንዲጠናቀቅ የሴቶች ድርሻ የጎላ መሆን አለበት ሲሉ አንዳንድ ያነጋገርናቸው ሴት አመራሮች ገልፀዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የትምህርትና ስልጠና ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ‎ወ/ሮ ፀሀይ ወራሳ፤ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ነፃ፣ ሠላማዊ፣ ፍትሀዊና ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ማካሄድ ዋነኛ ግብ ነው በማለት ምርጫው ስኬታማ እንዲሆን ሴቶች በግንባር ቀደምነት በመሳተፍ የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

‎ለሀገር ግንባታና ሠላም የሴቶች ድርሻ የጎላ መሆኑን የ6ኛው ጠቅላላ ምርጫ ማሳያ ነው ያሉት ኃላፊዋ፤ ሀገራችን ወደ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሀገሮች ተርታ እንድትሰለፍና የብልፅግና ተምሳሌት እንድትሆን መሥራት ይጠበቅብናል ሲሉም አመላክተዋል።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ‎ወ/ሮ ተስፋነሽ ጥላሁን፤ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ነፃ፣ ሠላማዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የምክር ቤት አባላትና ሴቶች በተገቢው ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል በማለት ሀሳባቸውን ሰንዝረዋል።

‎የወናጎ ወረዳ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፍሬነሽ ሮባ በበኩላቸው፤ ለምርጫ ሂደት ውጤታማነት በ6ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሴቶች ተሳትፎ የነበሩ ጥንካሬዎችን በመውሰድና ጉድለቶችን በማረም በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሴቶችን ተሳትፎ በላቀ ደረጃ አጠናክሮ ማስቀጠል ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል።

‎ዘጋቢ: ፅጌ ደምሴ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን