መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ መንግስት የግል ጤና ተቋማትን በማስፋፋት ረገድ ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን እየሰራ ነው – የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ

መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ መንግስት የግል ጤና ተቋማትን በማስፋፋት ረገድ ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን እየሰራ ነው – የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ

ሀዋሳ፡ ጥር 21/2016 ዓ.ም (ደሬቴድ) መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ መንግስት የግል ጤና ተቋማትን በማስፋፋት ረገድ ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ገልጿል፡፡

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የግል ጤና ተቋማት ክልላዊ ማህበር ምስረታ የአበላት ጉባዔ በሆሰዕና ከተማ ተካሄዷል፡፡

የጤና አገልግሎትን ለማጎልበት እና ጤናማ ትውልድን ለማፍራት በሚደረገው ጥረት የግል ጤና ተቋማት ድርሻ ከፍተኛ ነው፡፡

በጉባኤው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ የግብአት እና ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካ አለሙ እንደገለጹት፤ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ መንግስት የግል ጤና ተቋማትን በማስፋፋት ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን እየሰራ ይገኛል፡፡

በጤናው ዘርፍ የግል ባለሀብቶች ሚናን በማሳደግ እና የግል ጤና ተቋማትን ለማስፋፋት ምቹ ሁኔታ በመፍጠር የበርካታ ዜጎችን ህይወት መታደግ መቻሉን ገልፃዋል፡፡

የግል ጤና ተቋማት ለስፋፋት ህግ እና ስረዓትን በመከተል አስፈላጊ የአቅርቦት እገዛ በማድረግ መንግስት እየሰራ መሆኑን ያነሱት ዳይሬክተሩ በክልሉ ከ1ሺህ 2 መቶ በላይ ባለሀብቶች ፍቃድ አግኝተው በግል ጤና ተቋማት አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ ብለዋል፡፡

በዘርፉ በስነ-ምግባር የታነፃ ባለሙያ በመፍጠር ብቁና ጥራት ያለቸው አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ለማስፋፋት እንደሚሰራም አክለዋል፡፡

የሀዲያ ዞን የግል ጤና ተቋማት አስተባበሪ እና የክልሉ የግል ጤና ተቋማት ማህበር በፕሬዝዳንትነት የተመረጡት አቶ አለማየው ተረፈ በበኩላቸው የግል ጤና ተቋማት ማህበር ለትርፍ እና ለንግድ ሳይሆን የጤና አገልግሎት ተደረሽ ለማድረግ የሚሰሩ ተግባራትን በማገዝ ህዝብ እና መንግስትን የሚያገለግል ተቋም መሆን ይጠበቃል ብለዋል፡፡

ማህበሩን ለማሳደግ እና በጤናው ዘርፍ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል ከስራ አስፈፃሚ ኮሚቴዎች እና ከአበላቱ ብዙ የሚጠበቅ መሆኑን ገልፃው ምቹ አካባቢውን ከማመቻቸት ጀምሮ በማገዝ ህዝብን እንዲያገለግሉ ማድረግ ቀዳሚ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በጉባኤው የማህበሩ የቀጣይ የሥራ አቅጣጫና ከአባላቱ ጥያቄ ተነስቶ ማብራሪያ የተሰጠ ሲሆን 9ኝ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴዎችን በመምረጥ ጉባኤው ተጠናቋል፡፡

ዘጋቢ: ሳጅዳ ሙደስር – ከሆሳዕና ጣቢያችን