የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመፍታት የቤት ልማት አቅርቦት ወሳኝ መሆኑ ተገለፀ‎

የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመፍታት የቤት ልማት አቅርቦት ወሳኝ መሆኑ ተገለፀ‎

‎በጌዴኦ ዞን የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ለበርካታ ዘመናት ለነበሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እየሰራ መሆኑን አስታውቋል።‎

‎በመርሀ ግብሩ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የይርጋጨፌ ከተማ ከንቲባ አቶ ብዙአየሁ ታደሰ፤ ከተማውን ለመቀየር በርካታ የልማት ፕሮጀክቶች እየተሠሩ ካሉት መካከል አንዱ የቤቶች ልማት ግንባታ መሆኑን አንስተዋል፡‎

‎የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለመፍታት የቤቶች ልማት አቅርቦት ወሳኝ ነው ብለው፤ የተገነቡ ቤቶችም ደረጃቸውን የጠበቁ፣ ለኑሮ ምቹና የተሟላ የመሠረተ ልማት አገልግሎት ያለበትና ከቀድሞ የተሻሉ መሆኑን ከንቲባው አብራርተዋል።‎

‎የተገነቡ ቤቶች የከተማዋን የኢንቨስትመንት፣ የገቢ ዕድገትና አቅም ለማሳደግና ከተማዋን ለማልማት ያስችል ዘንድ ለልማት ተነሺ ለሆኑና ለበርካታ ጊዜ የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ለነበረባቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ቤቶቹ የሚሠጡ መሆኑን ከንቲባው አብራርተዋል።‎

‎በመሆኑም ከኢፍትሃዊነት በፀዳ መልኩ የቤቶቹ ዕደላ በዕጣ የሚተላለፍ መሆኑን አቶ ብዙአየሁ አስረድተዋል።‎

‎የይርጋጨፌ ከተማ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ሀላፊና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ሆርዶፋ እንደገለፁት፤ ለማህበረሰቡ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠትና ከተማዋን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ በትኩረት እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል።‎

‎እንደሀገር ከተጀመሩ ኢንሼቲቮች መካከል አንዱ የቤቶች ልማት ፕሮጀክት በመሆኑ እንደ ከተማ አርባ ቤቶችን በአርባ ቀን ገንብተው ማስተላለፍ መቻላቸውን አንስተዋል።‎

‎በመርሀ ግብሩ የተገኙ ታዛቢዎችም በተለይም ምርጫውን በሠላም በተሳካ ማግስት የማህበረሰቡን የመልካም አስተዳደር ችግር ለመፍታት በተደረጉ ተግባራት መደሰታቸውን አመላክተዋል።‎

‎ዘጋቢ: ፅጌ ደምሴ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን