‎‎የጌዴኦ ዞን አስተዳደር የጌዴኦን ተፈጥሮአዊና ባህላዊ መልክዓ-ምድር በመንከባከብ፣ አካባቢውን ለቱሪስት መስህብና ለኢኮኖሚ እድገት ለማዋል በትኩረት እየሰራ ነው‎‎‎ሀዋሳ፡ መጋቢት 10/2018 (ደሬቴድ)‎የጌዴኦ ዞን አስተዳደር የጌዴኦን ተፈጥሮአዊና ባህላዊ መልክዓ-ምድር በመንከባከብ፣ አካባቢውን ለቱሪስት መስህብና ለኢኮኖሚ እድገት ለማዋል በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጿል፡፡

ዞኑ ይህን በዩኔስኮ የተመዘገበ ዓለም አቀፍ ቅርስ በዘላቂነት ለመጠበቅ እንዲቻል ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ አካሂዷል፡፡


የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ ምድር ቅርስ ሰውና ተፈጥሮ ተዋህዶ መኖር  እንደሚችል የሚያሳይ በመሆኑ በዩኔስኮ  መመዝገቡ አንዱ ማሳያ መሆኑን  የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡


‎ተፈጥሮ የቸረችውን ውብና ፀጋ  ቅርስ ከአደጋ በመታደግ እና በዘላቂነት በመጠበቅ የቱሪስት መዳረሻና የኢኮኖሚ  ምንጭ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አስተዳዳሪው አብራርተዋል ።

‎የዓለም ቅርስ ሆኖ የተመዘገበው መልክዓ ምድሩ ባህላዊ እሴቱን ሳይለቅ  ለቀጣዩ ትውልድ  የማሻገር ስራ እየተሠራ  እንደሚሀኝ የገለፁት አስተዳዳሪው ለውጤታማነቱ  ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል።



‎የዞኑ ቱሪዝም  መምሪያ  ኃላፊው  አቶ እድሉ ታደሰ አባቶች በትውልድ ቅብብሎሽ ጠብቀው ያቆዩትን ቅርስ በመንከባከብና በመጠበቅ ወደ ትውልድ  ለማሻገር ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል ።


‎በመድረኩ የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ሕይወት ኃይሉ፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ወይንቱ መልኩ፣ የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር)  ጨምሮ የክልል ምክትል የቢሮ ኃላፊዎችና ሌሎችም የሚመለከታቸው  አካላት  ታድመዋል ።


‎ዘጋቢ: ፅጌ  ደምሴ – ከይርጋጨፌ  ጣቢያችን