በኮሬ ዞን የ2018 ዓ/ም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በይፋ ተጀመረ

በኮሬ ዞን የ2018 ዓ/ም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በይፋ ተጀመረ

ሀዋሳ፡ ጥር 18/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) በኮሬ ዞን የ2018 ዓ/ም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በዞኑ ጎርካ ወረዳ ከረዳ ቀበሌ በጋርከይንዶ ተፋሰስ ላይ በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀምሯል።

የኮሬ ዞን ዋና አስተዳደር አቶ ታረቀኝ በቀለ በዚህ ወቅት እንዳሉት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ አስፈላጊነቱን በመገንዘብ በልዩ ትኩረት ማከናወን ይጠበቅብናል።

ከአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ጎን ለጎን የበልግ እርሻ ዝግጅት ማጠናከር አስፈላጊ እንደሆነ ገልፀው ለ30 ቀን በሚቆየው የፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ሁሉም ህብረተሰብ በነቂስ ወጥቶ እንዲሳተፍ ጠይቀዋል ።

የኮሬ ዞን ምክትል አስተዳደርና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አስታረቀኝ አንዳባ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እርጥበትን ይዞ በማቆየት ለልማት ትሩፋትና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ ነው የተናገሩት ።

በዘንድሮ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ በዞኑ ከ 2ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት እንደሚለማ የገለፁት ኃላፊው ለአየር ንብረት የማይበገር አካባቢ ለመፍጠር በትጋት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል።

የጎርካ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ የሆኑት አቶ ተፈራ ቦንዶሮ በበኩላቸው አካባቢን ለማልማት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያለውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ሁሉም በየአካባቢው ማከናወንና ተጠቃሚ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል ።

በአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ማስጀመሪያ ላይ የተሳተፉ የአካባቢው ነዋሪዎችም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ የአፈር መሸርሸርን ለመከላከልና ለአካባቢ ልማት አስፈላጊ በመሆኑ ሁላችንም በኃላፊነት መስራት አለብን ብለዋል።

ዘጋቢ፡ ለምለም ኦርሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን