የደረሱ ሰብሎችን በወቅቱ እና ያለብክነት ሊሰበሰብ እንደሚገባ የባኮ ዳውላ ኣሪ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት አሳሰበ

የደረሱ ሰብሎችን በወቅቱ እና ያለብክነት ሊሰበሰብ እንደሚገባ የባኮ ዳውላ ኣሪ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት አሳሰበ

ከመኸር እርሻ ከ1ሺህ 479 ሄክታር 564 ሺህ 367 ኩንታል ምርት መሰብሰቡን የባኮ ዳውላ አሪ ወረዳ ግብርና ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡

አስተያዬታቸውን ከሰጡን መካከል አርሶ አደር አቶ ዘመሙ ባሳዝን እና አቶ መለሰ ድክስ እንደገለፁት በመኸር እርሻ በቴክኖሎጂ ጤፍ እና አደንጓሬ የዘሩት በጥሩ ሁኔታ ምርት ደርሶ እየሰበሰቡ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

ወቅቱ ምርት ለመሰብሰብ ምቹ ስለሆነ የደረሱት ሰብሎችን ከብክነት በጸዳ መልኩ ቤተሰቦቻቸውን አደራጅተው እየሰበሰቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በዘንድሮ መኸር እርሻ 5ሺህ 154 ሄክታር በዘር ለመሸፈን ታቅዶ 5ሺህ 178 ሄታክር በዘር ተሸፍኖ ምርት እየተሰበሰበ እንደሚገኝ የባኮ ዳውላ አሪ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጳውሎስ ባኖ ገልጸዋል፡፡

1ሺህ 479 ሄክታር ጤፍና አዴንጓሬ ለምርት ደርሶ 564 ሺህ 367 ኩንታል እንደተሰበሰበ ኃላፊው ገልጸዋል፡፡

በመኸሩ እርሻ መሬት በዘር በምሸፍንበት ወቅት እርጥበቱ አመች እንደነበረ ገልጸው፥ አሁንም ደረቃማው አየር ለደረሱ ሰብሎች ምቹ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

አርሶ አደሩ ለምርት የደረሱ ሰብሎችን ያለብክነት ምርታቸውን በመሰብሰብ የመኸር እርሻ በፀሐይ የተጎዳውን በማካካስ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ወደ መስኖ እርሻ እንዲገቡ ኃላፊ ጨምረው አሳስበዋል፡፡

ዘጋቢ፡ ታገል ለማ – ከጂንካ ጣቢያችን