በቡርጂ ዞን ለሚገኙ የተለያዩ አቅመ ደካማ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ተደረገ
ሀዋሳ፡ መስከረም 13/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) የቡርጂ ልማት ማህበር ከዞኑ የተለያዩ አከባቢዎች ለተወጣጡ አቅመ ደካማ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ።
በመረሃ ግብሩ የተገኙት የቡርጂ ዞን ብልፅግና ፓርት ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ኡሜ ቾኮል የትምህርት ዘርፍ የህልውና ጉዳይ ስለሆነ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ጠቁመው፥ ልማት ማህበሩ ህብረተሰቡን በማስተባበር ለሰራው የድጋፍ ማሰባሰብ ሥራ አመስግነዋል፡፡
የቡርጂ ልማት ማህበር የቦርድ ሰብሳቢ አቶ በርሱ ህርባዬ በበኩላቸው፥ የትምህርት ብክነት ለማስቀረት እና መጠነ ማቋረጥ ለመቀነስ ድጋፉ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸው፥ ትልቁ ግባችን የተደገፉ ተማሪዎች ትምህርታቸውን ጨርሰው ማየት ነው ብለዋል።
የቡርጂ ልማት ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ማርቆስ ጩሙኦ፥ በ5 ቀናት ወስጥ ከ47 ሺህ ብር በላይ ከህብረተሰቡ በማሰባሰብ 50 ለሚሆኑ ተማሪዎች ድጋፍ ማድረጋቸውን አንስተው ለጥያቄያቸው በጎ ምላሽ የሰጡ የህብረተሰብ ክፍሎችንም አመስግነዋል ።
ድጋፉ ከተደረገላቸው ተማሪዎች መካከል ተማሪ ብሌን ወየሳ እና ተማሪ ምርቃት አይላሞ በሰጡት አስተያየት የተደረገላቸው ድጋፍ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ የሚያደርግ በመሆኑ ደስተኞች መሆናቸውን አንስተው ድጋፉ ቀጣይነት እንዲኖረውም ጠይቀዋል፡፡
ዘጋቢ ፡ ቦጋለ ሉሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት ተደራሽ እንዲሆን ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተገለጸ
በክልሉ የተጀመረውን የልማት እና መልካም አስተዳደር ሥራዎችን በማጠናከር የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ከግጭት የጸዳ አካባቢ ለመፍጠር ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሠላም እና ፀጥታ ቢሮ አሳሰበ
በዘመናዊ መንገድ ንብ የማነብ ስራ በመጀመር ውጤታማ መሆናቸውን በወላይታ ዞን የዳሞት ወይዴ ወረዳ ወጣቶች ተናገሩ