በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርን ተግባራዊ በማድረጋቸው ተጠቃሚ መሆናቸውን በየኪ ወረዳ የኩቢጦ አካባቢ አርሶአደሮች ተናገሩ

በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርን ተግባራዊ በማድረጋቸው ተጠቃሚ መሆናቸውን በየኪ ወረዳ የኩቢጦ አካባቢ አርሶአደሮች ተናገሩ

በበልግና በመኸር ወቅት አርሶአደሮች በኩታ ገጠም በማረሳቸው ተጨባጭ ውጤት ማግኘታቸውን ባለድርሻ አካላት አረጋግጠዋል።

በሸካ ዞን የየኪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዳዊት ተሰማ፤ በዘንድሮ የምርት ዘመን በተዘረጋው ቅንጅታዊ አሰራር የአርሶአደሩን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ችለናል ብለዋል።

የምርት ዘመኑን ታሳቢ ያደረገ ምርጥ ዘር በቀረበው መሰረት አርሶአደሮች ተቀብለው በመስራታቸው ውጤታማ መሆናቸውን ያወሱት አቶ ዳዊት፤ መንግስት የዘረጋውን አሰራር በማስረጽ አካባቢያዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ቀጣይነት ያለው ስራ ይሰራል ብለዋል።

የየኪ ወረዳ ሳይት ደጋፊ እና የሸካ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ እምሩ ወዬሳ፤ ትጋት የታከለበት አሰራርን መተግበር ለውጤት እንደሚያበቃ ዘንድሮ በበልግና የመኸር ስራ ያመጣነው ውጤት አመላካች ነው ብለዋል።

የዞኑን እምቅ አቅም ማዕከል ባደረገ መልኩ አመራሩ፣ ባለሙያውና አርሶ አደሩ በቅንጅት መስራት ከቻሉ ለውጥና እድገት መሬት ላይ መኖሩን ተመልክተናል ብለዋል።

ዘንድሮ የBH-546 የበቆሎ ዝሪያ ከሌሎች የበቆሎ ዝርያዎች ጋር ሲነጻጸር እጅግ የላቀ ምርት እየሰጠ እንደሚገኝና በሁሉም አካባቢዎች ማስፋት እንደሚገባ አቶ እምሩ አውስተዋል።

የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አማኑኤል አለሙ፤ አርሶ አደሮች አዳዲስና ውጤታማ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀሙና የግብርና ምርታቸውን እንዲያሳድጉ እንደክልል በስፋት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

በሸካ ዞን የኪ ወረዳ የታየው የግብርና ስራ ለውጥ ለክልሉ ተሞክሮ የሚሆን ነው ያሉት ዳይሬክተሩ ቀጣይነት ያለው በምርምር የታገዘ ተጠቃሚነት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

ዘጋቢ፡ አስማማው ኃይሉ – ከማሻ ጣቢያችን