በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ የአርባምንጭ ደምና ህብረህዋስ ባንክ በ2017 በጀት አመት ከ6 ሺህ 378 ዩኒት በላይ ደም መሰብሰብ መቻሉን አስታወቀ

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ የአርባምንጭ ደምና ህብረህዋስ ባንክ በ2017 በጀት አመት ከ6 ሺህ 378 ዩኒት በላይ ደም መሰብሰብ መቻሉን አስታወቀ

‎ጠንካራ ተግባራትን በማጠናከር ጉድለቶችን በማረም በ2018 በጀት አመት ሰፊ ተግባራትን ለመከወን ማቀዱን ጠቁሟል፡፡

‎ጤና የሁሉም ነገር መሰረተ እንደመሆኑ በተለያዩ አጋጣሚዎች ለሚፈጠሩ ሰው ሰራሽ እና ድንገተኛ አደጋዎች የደም እጥረት ሲኖር የሌላ ሰው ደም በመጠቀም የሰዎችን ህይወት መታደግ እንደሚቻል የዘርፉ ምሁራን ያስረዳሉ፡፡

‎በአርባምንጭ ከተማ የደም ባንክ አገልግሎት የደም ለጋሾች ቡድን አስተባባሪ አቶ በሀይሉ ባሻ፤ በተጠናቀቀው በጀት አመት ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች አና ደም ለጋሽ ማህበራት በባለሙያዎች ሰፊ ርብርብ ደም መሰብሰብ መቻሉን ገልፀዋል፡፡

‎አቶ በሀይሉ አክለውም፤ ደም ለመለገስ የግንዛቤ ውስንነቶች እንደሚስተዋሉ ተናግረው ይህን ለመቅረፍ በተለያዩ መንገድ ለህብረተሰቡ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቶች እየተሰጡ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡

‎በ2017 በጀት አመት 9 ሺህ ዩኒት ደም ለመሰብሰብ የታቀደ ቢሆንም 6 ሺህ 378 ዩኒት ደም መሰብሰብ መቻሉን የገለፁት ደግሞ የአርባምንጭ ደም ባንክ ኃላፊ አቶ ኤርምያስ ባቤና ናቸው፡፡

በበጀት አመቱ 71 ከመቶ አፈፃፀምን ማሳካት ቢቻልም በርካታ ውስንነቶች አፈፃፀሙን ዝቅ እንዲል ምክንያቶች እንደነበሩ ጨምረው አብራርተዋል፡፡

‎በበጀት ዓመቱ የተከናወኑ ጠንካራ ተግባራትን በማጠናከር ተግዳሮቶችን በመቅረፍና የህብረተሰቡን የግንዛቤ ሁኔታዎች በመጨመር በቀጣይ ሰፊ ስራዎችን ለመስራት የባለድርሻ አካላት ትኩረትና ትብብር ሚናው የላቀ መሆኑን ገልፀዋል ኃላፊው።

‎በ2018 በጀት አመት የላቀ አፈፃፀም ለማስመዝገብ ቁርጠኛ መሆናቸውንም አመላክተዋል።

‎ዘጋቢ፡ ስምረት አስማማው – ከአርባምንጭ ጣቢያችን