ዜጎች የተሻለ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ማንኛውም ተግባር እንዲያሳልጡ መንግስት ከሚሠራው በተጨማሪ የልማት አጋር አካላት ተግባር ወሳኝ መሆኑን የኣሪ ዞን አስታወቀ

ዜጎች የተሻለ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ማንኛውም ተግባር እንዲያሳልጡ መንግስት ከሚሠራው በተጨማሪ የልማት አጋር አካላት ተግባር ወሳኝ መሆኑን የኣሪ ዞን አስታወቀ

በጂንካ ከተማ ሳፋሪ ኮም በይፋ ወደ ሥራ በሚገባበት መርሐ ግብር ላይ በመገኘት ነው የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ እና ከተማና መሠረተ ልማት መምሪያ ሀላፊ አቶ ገረመው ኃ/ማርያም ይህን የገለፁት።

የኢትዮጵያ ሕዝብ አዳዲስ ዲጂታል የቴክኖሎጂ አማራጮችን እንዲጠቀም ምቹ ሁኔታ መፍጠር በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ትልቅ አቅም ይፈጥራል ብለዋል።

ካምፓኒው በአካባቢው ለሚያደርገው ማስፋፊያና ሥራ የዞኑ አስተዳደር ድጋፍ እንደሚያደርግ አቶ ገረመው ገልጸዋል፡፡

የጂንካ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሲሳይ ጋልሺ እንደገለፁት፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዜጎች ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ሳፋሪ ኮም ትልቅ አቅም ይፈጥራል።

በቴሌኮም ዘርፍ ከግል አልፎ መንግስታዊ ሥራዎችን በተፋጠነ መልኩ በሚፈለገው ወቅት ለማከናወን የካምፓኒው ሥራ መጀመር ወሳኝ ነው ሲሉም አቶ ሲሳይ ገልፀዋል።

የሳፋሪ ኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሚር ዊም ቫን ሳፋሪ ኮም በጂንካና አካባቢው ሁሉም ሰው ቀልጣፋና ምቹ ኔትዎርክ እንዲጠቀም እየሠራ መሆኑን ገልፀዋል።

በከተማው 11 የኔትዎርክ ማሳለጫ ታዎሮች መዘርጋቱን ዋና ሥራ አስፈፃሚው ተናግረው፤ አገልግሎቱ በይፋ መጀመሩን አብስረዋል።

ለሥራው ስኬት አስተዋጽኦ ላበረከቱ የኣሪ ዞንና ጂንካ ከተማ አስተዳደርን አመስግነዋል።

ተቋሙ በአሁን ወቅት ከ1 መቶ በላይ ለሆኑ ዜጎች ሥራ ዕድል መፍጠሩን ሚር ዊም አብራርተው፤ በቀጣይ በአካባቢው የተለያዩ ልማታዊ ሥራዎችን ከመንግስት ጎን በመቆም እንደሚያከናውን ጠቁመዋል።

በይፋ ማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ ለጂንካ ከተማ አስተዳደር ጤናና ሌሎች ልማታዊ ሥራዎችን ማስፈፀሚያ ሳፋሪ ኮም 5 መቶ ሺህ ብር ድጋፍ አድርጓል።

ሳፋሪ ኮም በቴሌኮም ዘርፍ አዳዲስና ፈጣን አማራጮችን ይዞ በይፋ ሥራውን መጀመሩ የተገለፀ ሲሆን በቀጣይ በአካባቢው ማስፋፊያ ሥራዎችን እንደሚያካሂድ ነው የተብራራው።

ዘጋቢ: ተመስገን አበራ – ከጂንካ ጣቢያችን