በሸካ ዞን የኪ ወረዳ በቆ ቀበሌ በ36 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የገጠር ሞዴል መንደር ተመረቀ

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በሸካ ዞን የኪ ወረዳ በቆ ቀበሌ በ36 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የገጠር ሞዴል መንደር ተመርቆ ለተጠቃሚዎች ተላልፏል።

የሸካ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ በላቸው ጋራ በወቅቱ እንዳሉት፤ ከለውጡ ማግስት ጀምሮ የዞኑ አስተዳደር የህዝቡን የልማትና መልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልፀው የገጠር ሽግግር በማረጋገጥ የህብረተሰቡን አኗኗር ለመቀየር ሞደል መንደሩ ተገንብቷል።

የክልሉ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊና የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ፍቅሬ አማን፤ ብልፅግና ፓርቲ ለህዝቡ ቃል ከገባላቸው አንዱ መሠረተ ልማቶችን በማጠናቀቅ አዳዲስ የመሠረት ድንጋዮችን በማስቀመጥ የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ መመለስ መሆኑን ተናግረዋል።

በመደመር መንግሥት የህዝቦችን የሰላምና የልማት ጥያቄዎችን በመመለስ የተፈጥሮ ፀጋዎችን በመጠቀም የህዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥን ትኩረት ያደረገ መሆኑን አንስተዋል።

የገጠር ሞዴል መንደር የገጠር ሽግግር ጉዞ የሚያቀላጥፍና በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ አስተዋጽኦ የሚያበረክት እንደሆነም አመላክተዋል።

ሞደል መንደሩ በውስጡ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የያዘ መሆኑን አንስተው መንግሥት የገጠሩን ማኅበረሰብ ኑሮ በማሻሻል የገጠር ሽግግርን ለማሳካት ልዩ ኢንሼቲቭ ቀርጾ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

የአርሶ አደሩን ኑሮ ለማሻሻል የገጠር ሞደል መንደር ሀሳብ ተግባራዊ ከሆነ ጀምሮ በክልሉ 16 የገጠር ሞደል መንደር በመገንባት እያስተላለፈ መሆኑን ገልፀው መሠል የኑሮ ዘይቤን መከተል ያስፈልጋል ብለዋል።

የየኪ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ተሰማ፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ በወረዳው የህብረተሰቡን የአኗኗር ዘይቤን የሚለውጥ እንደሆነና ዘመናዊ መንደር ተግንብቶ ለምረቃ በመድረሱ ለዚህ ድጋፍ ላደረጉ ባለድርሻ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።

በ36 ሚሊየን ብር ወጪ ግንባታው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗልም ብለዋል።

የቤት ባለቤት የሆኑት የገጠር ሞደል መንደር ተጠቃሚዎች በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል የሚከተሉት የኑሮ ዘይቤ ዘመናዊ ያልሆና አስቸጋሪ እንደነበር አስታውሰው መንግስት በሰጣቸው ዕድል ዘመናዊ ሁሉን አቀፍ አገልግሎት ያሟላ ቤት ባለቤት ተጠቃሚ በመሆናቸው መደሰታቸውን ገልፀዋል።

ዘጋቢ: በዛብህ ታደሰ – ከማሻ ጣቢያችን