የክልሉ መንግስት ያወጣቸው የፋይናንስ አስተዳደር አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎችን ተፈጻሚ በማድረግ ላይ የሚታዩ ችግሮችን መቅረፍ እንደሚያስፈልግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ገለጸ

የክልሉ መንግስት ያወጣቸው የፋይናንስ አስተዳደር አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎችን ተፈጻሚ በማድረግ ላይ የሚታዩ ችግሮችን መቅረፍ እንደሚያስፈልግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ገለጸ

ሀዋሳ፣ ሰኔ 06/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) የክልሉ መንግስት ያወጣቸው የፋይናንስ አስተዳደር አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎችን ተፈጻሚ በማድረግ በሒሳብ አያያዝ፣ በግዢና ንብረት አስተዳደር ላይ የሚታዩ ችግሮችን መቅረፍ እንደሚያስፈልግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ገልጿል።

ቢሮው ለአየር ንብረት ለውጥና መሬት አስተዳደር ፕሮግራም አስተባባሪዎች፣ ለወረዳ ፋይናንስ ፎካሎች፣ ለግዢ ባለሙያዎች እና ለህብረት ስራ ኦዲተሮች 2ኛ ዙር ሥልጠና በወልቂጤ ከተማ እየሰጠ ነው።

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ በመንግስት ፋይናንስ ዘርፍ የቻናል አንድ ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ታረቀኝ ኑራሙ እንዳሉት የአየር ንብረት ለውጥና መሬት አስተዳደር ፕሮግራም በአለም ባንክና በፌደራል መንግስት የበጀት ድጋፍ የሚተገበር ፕሮግራም ሲሆን በአየር ንብረት ለውጥና መሬት አስተዳደር ላይ ትኩረት አድርጎ የሚሰራ ፕሮግራም ነው።

የፕሮግራሙ የፋይናንስ አጠቃቀምና አስተዳደር ሥርዓት የመንግስትን የሒሳብና የበጀት አስተዳደር ሥርዓትን በተከተለ መልኩ መፈጸም እንዳለበት የተናገሩት አቶ ታረቀኝ ሥልጠናው የሒሳብ፣ የግዢና የኦዲተር ባለሙያዎች የክልሉ መንግስት ያወጣቸው የፋይናንስ አስተዳደር አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎችን ተፈጻሚ በማድረግ በኩል ያለባቸውን ክፍተት ለመሙላት እንደሚረዳ ገልጸዋል።

በዚሁ በሁለተኛው ዙር ሥልጠና ከስልጤ፣ ከሀዲያና ከከምባታ ዞኖች  የተወጣጡ የፕሮግራሙ አስተባባሪዎችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛል።

ዘጋቢ፣ ተረፈ ሀብቴ ከወልቂጤ ጣቢያችን