በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጂንካ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ለ23ኛ ዙር በተለያዩ የሙያ መስኮች በመደበኛና በማታ መርሃ ግብር ያሰለጠናቸውን 347 ተማሪዎችን አስመረቀ

ተመራቂዎች በቀሰሙት ዕውቀትና ሙያ ሥራ በመፍጠር ማህበረሰቡን ሊያገለግሉ እንደሚገባም ተገልጿል።

የጂንካ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ እቶ ደግፌ ጌታቸው የእንኳን ደስ አላችሁ መልክት አስተላልፈው፤ ኮሌጁ የተማረ የሰው ኃይልና የተለያዩ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ውጤቶችን በማፍለቅ ለከተማው ዕድገት እያበረከተ ያለውን አስተዋጽኦ አድንቀዋል።

የኣሪ ዞን ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊና ዋና የመንግስት ተጠሪ አቶ አፌዶ ወርቁ በበኩላቸው፤ የኮሌጁ ምሩቃን ባገኙት ዕውቀትና ሙያ በገበያ ተወዳዳሪ የሚያደርጋቸውን ሥራ በመፍጠር ራሳቸውንና ማህበረሰቡን እንዲያግዙ አሳስበዋል፡፡

የጂንካ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲን አቶ ካሳሁን ጌታቸው፤ ኮሌጁ በተለያዩ የሙያ መስኮች ብቁና ተነሳሽነት ያላቸውን አምራች ዜጋ እያፈራ እንደሚገኝ ገልፀው በመደበኛና በማታ መርሃግብር የተማሩ ወንድ 166 ሴት 181 በጠቅላላው 347 ተማሪዎች ለምረቃ መብቃታቸውን አብራርተዋል።

ኮሌጁ በኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽንና በቴክኖሎጂ ሽግግር ሥራ 775 ነባርና ለ312 አዲስ ማህበራት በጠቅላላው ለ1 ሺህ 87 ማህበራት አንቀሳቃሾች የክህሎት፣ የዕውቀት፣ የካይዘንና የኢንተርፕርነርሽፕ ስልጠና በመስጠት ውጤታማ መሆኑን አክለዋል።

ተመራቂ ተማሪዎች በበኩላቸው፤ በቀሰሙት እውቀት ሥራ በመፍጠር ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን በቅንነት ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

በትምህርት ዘመኑ በኮለጁ የተሠሩ ምርታማነትን የሚያሳድጉ የፈጠራና የቴክኖሎጂ ሥራዎች ጉብኝት የተደረገ ሲሆን ከተለያዩ የትምህርት ክፍሎች የተሻለ ውጤት ላስመዘገቡ ሰልጣኞች የሜዳሊያና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

ዘጋቢ፡ ተመስገን አሰፋ – ከጂንካ ጣቢያችን