ሚዲያን ለአዎንታዊ ነገር በመጠቀም ወጣቱ ሀገርን መገንባት አለበት – የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን

ሚዲያን ለአዎንታዊ ነገር በመጠቀም ወጣቱ ሀገርን መገንባት አለበት – የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን

ሀዋሳ፡ ነሐሴ 09/2018 ዓ.ም (ደሬቴድ) ሚዲያን ለአዎንታዊ ነገር በመጠቀም ወጣቱ ሀገርን መገንባት አለበት ሲል የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

‎የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዲላ ከተማ ከ1 መቶ 50 በላይ ለሚሆኑ የሚዲያ ባለሙያዎችና ወጣቶች ስልጠና እየሰጠ ነው።

‎በስልጠናው ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ በዲጂታል ዓለም ውስጥ ሚዲያ ያለው ተጽዕኖ የጎላ ነው።

‎ሚዲያን ለሀገር ግንባታ የተጠቀሙ ሀገራት ሀገራቸውን እየገነቡ ናቸው ያሉት አስተዳዳሪው፤ ይህን የሚደግፉ ወጣቶችን ማፍራት አስፈላጊ ነው ብለዋል።

‎እሴቶቻችንን ሊሸረሽሩ የሚችሉ መረጃዎችን ወጣቶች በጋራ መከላከልና በአቅም ግንባታው ዘርፍ የተጀመሩ ተግባራትም መጠናከር እንዳለባቸው አሳስበዋል።

‎የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ምስራቅ ጌቱ እንደገለጹት፤ ስልጠናው የሚዲያና የዲጂታል መረጃ አጠቃቀም ክህሎትን ለማሳደግ፣ የተሳሳተ መረጃን ለማጣራት እና ማህበራዊ ሚዲያን ለልማትና ለአገር ግንባታ ለመጠቀም የሚያግዝ ነው።

‎ባለስልጣኑ በተሰጠው ስልጣን የአቅም ግንባታ ላይ እየሠራ ነው ብለው፤ ሚዲያን ለአዎንታዊ ነገር በመጠቀም ወጣቱ ሀገር መገንባት እንዳለበት አሳስበዋል።

‎ባለስልጣኑ ከስልጠናው ጎን ለጎን በተለያዩ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ድጋፍ የሚያደርግ ይሆናልም ተብሏል።

‎ከመገናኛ ብዙሃን ባለስልጣኑ ፈቃድ ያገኙ 3 መቶ 29 ሚዲያዎችንና ከ2 ሺህ 5 መቶ በላይ የማስታወቂያ ድርጅቶችንና ሌሎችንም የሚያስተዳድር ተቋም መሆኑ ተመላክቷል።

‎ዘጋቢ: እስራኤል ቅጣው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን