በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል እየተከናወነ እንደሚገኝ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ገለፀ
በበጀት አመቱ ያልተጠናቀቁ የልማት ስራዎች በቀጣይ በጀት አመት አጠናክሮ ለመስራት ያለመ የፓናል ውይይትና የመስክ ጉብኝት በወልቂጤ ከተማ ተካሂዷል።
በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተማ ልማትና ኢንዱስትሪ ክላስተር አስተባሪና የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደ ሚካኤል በዚህ ወቅት እንደገለፁት በክልሉ የተጀመሩ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትል ስራ በተጠናከረ መልኩ እየተሰራ ይገኛል።
ሀላፊው አክለውም በበጀት አመቱ ያልተጠናቀቁ የልማት ስራዎች በቀጣይ በጀት አመት በተጠናከረ ሁኔታ ለማከናወን ያለመ የመስክ ጉብኝት መደረጉን አስረድተዋል።
በክልሉ በኮሪደር ልማት በተለያዩ ከተሞች በሁለት ምዕራፍ ከ165 ኪሎ ሜትር በላይ ለመስራት በማቀድ ወደ ተግባር መገባቱን በማንሳት በመጀመሪያው ምዕራፍ ከ115 ኪሎ ሜትር በላይ ለማጠናቀቅ እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በጉራጌ ዞን ከ171 ሚሊየን ብር በላይ በመመደብ የኮሪደር ልማት ስራዎች መጀመራቸውንና አፈጻጸማቸው ጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የዞኑ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ሀላፊ አቶ ታምራት ውድማ ገልጸዋል።
በኮሪደሩ ልማቱ 25 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የመንገድ መሰረተ ልማት እንዲሁም የወጣቶች መዝናኛ አረንጓዴ ስፍራዎችን መስራት የፕሮጀክቱ አካል መሆኑን አቶ ታምራት ተናግረዋል።
በዞኑ በተያዘው በጀት አመት 15 ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንና ከነዚህም 9 ፕሮጀክቶች አፈጻጸማቸውን 90 በመቶ ማድረስ መቻሉን ጠቁመዋል።
የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት በከተማው የተጀመሩ የልማት ስራዎች ላይ ህብረተሰቡን በማሳተፍ አመርቂ ውጤቶች እየታዩ ነው።
በከተማው የተጀመረው የአስፓልት መንገድ ማስፋትና የውስጥ ለውስጥ አስፓልት ስራ በፍጥነት ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል።
በከተማው ከተጎበኙ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ የወልቂጤ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት ግንባታ ሲሆን ህንጻው ከተያዘለት ጊዜ ቀደም ብሎ በማጠናቀቅ ለህብረተሰቡ አገልግሎት እንዲሰጥ ለማስቻል እየተሰራ እንደሚገኝ የህንጻው ተቋራጭ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ ዮሀንስ ጌታቸው ተናግረዋል ።
ዘጋቢ ፡ዳዊት ዳበራ-ከወልቂጤ ጣቢያችን
More Stories
የክልሉ መንግስት ያወጣቸው የፋይናንስ አስተዳደር አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎችን ተፈጻሚ በማድረግ ላይ የሚታዩ ችግሮችን መቅረፍ እንደሚያስፈልግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ገለጸ
በሲዳማ ክልላዊ መንግስት ገቢዎች ባለስልጣን “ታማኝ ግብር ከፋይ ብርቱ የልማት አርበኛ ነው” በሚል መሪ ቃል ለታማኝ ግብር ከፋዮች እውቅና የሚሰጥ መድረክ እየተካሄደ ነው