ቡና ባንክ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ ከግብር በፊት 1ነጥብ 19 ቢሊየን ብር አተረፈ

የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ መጠንም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ6 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር ማደጉን የቦርዱ ሊቀመንበር አምባሳደር ዓለማየሁ ሰዋገኝ ጠቁመዋል፡፡

በዚህም የባንኩን አጠቃላይ የተቀማጭ ገንዘብ መጠን በ32 ነጥብ 8 በመቶ ከፍ በማድረግ 27 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር እንዳደረሰው ተነግሯል።

ከዚህ ውስጥ የቁጠባ ሂሳብ ተቀማጭ 77 ነጥብ 8 በመቶ የሚሆነውን ከፍተኛ ድርሻ እንደያዘ ነው ባንኩ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መረጃ የተመላከተው።

ባንኩ የኮቪድ 19 ወረርሽኝ፣ የሩሲያ ዩክሬን ጦርነትና በሀገሪቱ ተፈጥሮ የነበረው የጸጥታ ችግር በአገር ኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ያሳደሩትን መቀዛቀዝ ተቋቁሞ በአትራፊነት መቀጠል ስለመቻሉም ተገልጿል፡፡

ይህም ለባንኩ ባለአክሲዮኖችና ለአጠቃላይ ሰራተኞቹ የሚያበረታታ ውጤት ነው ተብሏል።