ሊቨርፑል ዎልቭስን በማሸነፍ መሪነቱን አጠናከረ
በ25ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የሊጉ መሪ ሊቨርፑል ዎልቭስን 2ለ1 በሆነ ውጤት በሜዳው በማሸነፍ መሪነቱን አጠናክሯል።
የሊቨርፑልን የማሸነፊያ ግቦች ሞሐመድ ሳላህ በፍጹም ቅጣት ምት እና ሉይዝ ዲያዝ በክፍት የጨዋታ እንቅስቃሴ በመጀመሪያው አጋማሽ ከመረብ አሳርፈዋል።
ዎልቭስን ከሽንፈት ያልታደገችውን ግብ ማቲያስ ኩና ከዕረፍት መልስ አስቆጥሯል።
ሞሐመድ ሳላህ ለሊቨርፑል በሁሉም ውድድሮች 28ኛውን በፕሪሚዬር ሊጉ ደግሞ 23ኛ ጎሉን አስቆጥሯል።
በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በፕሪሚዬር ሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች 101 አድርሷል።
አሌክሳንደር አርኖልድ በዛሬው ዕለት ለሊቨርፑል 250ኛ ጨዋታውን አከናውኗል። በዚህም በትንሽ ዕድሜው ይህን ያኽል ጨዋታን በማከናወን በክለቡ ፈር ቀዳጅ ሆኗል።
የመርሲሳይዱ ክለብ ማሸነፉን ተከትሎ ከተከታዩ አርሰናል በ7 ነጥብ በመራቅ 60 ነጥብ በመያዝ ሲመራ ዎልቭስን በ19 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ፕሪሚዬር ሊጉ መካሄዱን ሲቀጥል የሳምንቱ የመጨረሻው እና ተጠባቂው ጨዋታ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ በቶትናም ስታዲየም ማንቸስተር ዩናይትድ እና ቶትንሃም ይጫወታሉ።
ዘጋቢ፡ ሙሉቀን ባሳ
More Stories
ሀገር አቀፍ የክለቦች ሻምፒዮና ውድድር ያለምንም ችግር እንዲካሄድ በቂ ዝግጅት መደረጉን የኣሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ ገለፁ
ዳራማሎ ደንዳሾ ስፖርት ክለብ ባስኬት ቡናን በማሸነፍ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ክለቦች ሻምፒዮና የዋንጫ አሸናፊ ሆነ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ክለቦች ሻምፒዮና ዛሬ በተደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ለፍፃሜ ያለፉ ክለቦች ተለይተው ታውቀዋል