ሀዋሳ ከተማ ሙሉጌታ ምህረትን የክለቡ አሰልጣኝ አድርጎ ሾመ

ሀዋሳ ከተማ ሙሉጌታ ምህረትን የክለቡ አሰልጣኝ አድርጎ ሾመ

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬርሊግ ከተመሰረተ ጊዜ አንስቶ በሀገሪቱ ዋናው የሊግ እርከን እየተወዳደረ የሚገኘው ሀዋሳ ከተማ የቀድሞ ተጫዋቹን እና አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረትን የክለቡ ዋና አሰልጣኝ አድርጎ ሾሟል።

ከውጤት መጥፋት ጋር ተያይዞ አሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉን ያሰናበተው ሀዋሳ ከተማ በግዚያዊው አሰልጣኝ ወንድማገኝ ተሾመ ሲመራ ከቆየ በኋላ በዛሬው ዕለት ዋና አሰልጣኙን አሳውቋል።

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬርሊግ ዋንጫን በማንሳት ቀዳሚው የክልል ክለብ የሆነው ሀዋሳ ከተማ በ2017 የመጀመሪያው የውድድር ዘመን አጋማሽ
በከፍተኛ ደረጃ የውጤት ማጣት አጋጥሞት ይገኛል።

ክለቡ በፕሪሚዬርሊጉ 17 ጨዋታዎችን አከናውኖ 3 ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ በ8 ጨዋታዎች ተሸንፎ እና 6 መርሐግብሮችን በአቻ ውጤት አጠናቆ በ15 ነጥብ በወራጅ ቀጠናው 17ኛ ደረጃ ላይ ሆኖ የመጀመሪያውን የውድድር ዘመን አጋማሽ አጠናቋል።

አዲሱ አሰልጣኝ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬርሊግ ክለቡን ማቆየት ትልቁ የቤት ስራው እንደሆነም ከክለቡ የማህበራዊ ትስስር ገፅ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምሕረት ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ምክትል አሰልጣኝነት፣ በሀዋሳ ከተማ በምክትል እንዲሁም በዋና አሰልጣኝነት ያገለገለ ሲሆን በማስከተል በሀዲያ ሆሳዕና እና ወልቂጤ ከተማ መሥራቱ ይታወቃል።

እንዲሁም በእግርኳስ ተጫዋችነት ዘመኑ ደግሞ በሀዋሳ ከተማ ፣ ደደቢት እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫውቶ አሳልፏል።

በሙሉቀን ባሳ