ሕዳር 29 የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች በጋራ በመሆን በባህልና እሴቶቻቸው ደምቀው በአንድነት የሚያከብሩት ልዩ ቀን ነው – የኮሬ ዞን አስተዳደር
ሀዋሳ፡ ሕዳር 17/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) ሕዳር 29 የኢፌዲሪ ህገ-መንግስት የጸደቀበትና የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች በጋራ በመሆን በባህልና እሴቶቻቸው ደምቀው በአንድነት የሚያከብሩት ልዩ ቀን ነው ሲል የኮሬ ዞን አስተዳደር ገለጸ፡፡
በኮሬ ዞን “ብዝሃነትና እኩልነት ለሀገራዊ አንድነት” በሚል መሪ ቃል 19ኛው የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን ተከብሯል።
በበዓሉ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የኮሬ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታረቀኝ በቀለ እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ የጋራ ቀን ብሄር ብሄረሰቦች የብዝሃ ማንነታቸውን የሚያጎለብት፣ አብሮነታቸውን የሚያጸኑበት እና አንድነታቸውን የሚያጠናክሩበት ነው፡፡
የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል ቀንን ከማክበር ጎን ለጎን ሙስናን ለመከላከል ግለሰቦች፣ የመንግስትና የሃይማኖት ተቋማትን ጨምሮ ሁሉም የድርሻቸውን መወጣት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።
የኮሬ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ ወ/ሮ አካላት በቀለ በበኩላቸው፤ የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን የኢትዮጵያ ህዝቦች ማንነታቸው እንዲከበር፣ ለፍትህና ለዴሞክራሲ ብሎም ለነፃነት ሥርዓት መረጋገጥ ጠንክረው እንዲሠሩ የሚነሳሱበትን መሠረት የጣለ ቀን እንደሆነ ተናግረዋል።
የዘንድሮው የኢትዮጵያን የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በተለያዩ ኩነቶች ባለፉት ሁለት ሳምንታት እየተከበረ እንደቆየ ገልጸው በዛሬው ዕለት የማጠቃለያ ፕሮግራም መካሄዱን ተናግረዋል።
በፕሮግራሙ ላይ በፌደራሊዝም ስርዓቱ ላይ ያተኮረ ሰነድ በአቶ ደምሴ አየለ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።
ዘጋቢ፡ ለምለም ኦርሳ – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የሴቶች ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ በስፖርትና ባህል ልማት ዘርፍ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ለማሳደግ አበክሮ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
ህግና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የክልሉን ፍትህ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት ሥራ አፈፃፀም አደመጠ
ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እንደሚሠራ የዲላ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ