ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እንደሚሠራ የዲላ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ
ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እንደሚሠራ የዲላ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ
”ዳራሮ ለባህልና ለቱሪዝም ልማት” በሚል መሪ ቃል በሚከበረው የዳራሮ በዓል የ2 ነጥብ 5 ቢልዮን ብር የልማት ፕሮጀክቶች የዳራሮ ብስራቶች መርሃ ግብር ተካሂዷል።
የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉት የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን ደምሴ (ዶ/ር)፤ ሀገራችን የበርካታ ባህልና እሴት ባለቤት መሆኗንና የሰላም፣ የፍቅርና አንድነት ነጸብራቅ የሆነው የዳራሮ በዓልም ለዚህ ማሳያ መሆኑን አመላክተዋል።
”ዳራሮ ለባህልና ቱሪዝም ልማት” በሚል መሪ ቃል የሚከበረው የዳራሮ በዓልን ከልማት ጋር ለማስተሳሰር በምንሠራው ሥራ ከህዝቡ ጋር ከተማችንን ለነዋሪዎች ምቹና ውብ ለማድረግ እንሠራለን ብለዋል።
የ5 ኪሎ ሜትር አስፓልት መንገድ፣ ባለ ሰባት ወለል የአስተዳደር ህንጻ፣ የወንዝ ዳርቻ ልማትና የከተማዋን ገጽታ የሚቀይሩ የአደባባይ ኮሪደር ፕሮጀክቶች የሚሠሩ መሆናቸዉን ተናግረዋል።
ፕሮጀክቶቹ ከ2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ የሚፈጁ መሆናቸውን ገልጸው፤ ከህዝቡ ጋር የሚፈጸም ይሆናል ብለዋል ዶ/ር መስፍን።
የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ፕሮጀክቶቹ ከተማዋን የቱሪዝም እና የኮንፈረንስ ማዕከል ያደርጋታል ብለዋል።
የዲላ ከተማ ከተቆረቆረች ከ1 መቶ 20 ዓመታት በላይ ያስቆጠረች ቢሆንም በተፈለገው ልክ አለማደጓንና አሁን የሚጀመሩ ፕሮጀክቶች ከተማዋን ከፍ የሚያደርጉና በመንግስት ሀብት ብቻ የሚፈጸሙ ባለመሆናቸው በጋራ ተባብረን ዲላን ማልማት ያስፈልገናል ብለዋል።
ዳራሮ ከባህላዊነት ባሻገር ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳን እያመጣ መሆኑንም አስተዳዳሪው አመላክተዋል።
ዘጋቢ: እስራኤል ቅጣው – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን

More Stories
የመሠረተ ልማት ችግሮችን ለመቅረፍ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተገለጸ
በአከባቢዉ የሚስተዋለውን የምርጥ ዘር እጥረት ችግር ለመቅረፍ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው
የአከባቢን እና የሀገርን ሰላም ለማረጋገጥ የሚቻለው ህብረተሰቡን የሰላም ባለቤት ማድረግ ሲቻል መሆኑ ተገለጸ