በጤናው ዘርፍ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥ ተግባራትን ለማስቀረትና ማህበረሰቡ ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኝ ለማስቻል እየተሰራ ነው – የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ

በጤናው ዘርፍ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥ ተግባራትን ለማስቀረትና ማህበረሰቡ ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኝ ለማስቻል እየተሰራ ነው – የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ

ሀዋሳ፡ ጥቅምት 07/2017 ዓ.ም (ደሬቴድ) በጤናው ዘርፍ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥ ተግባራትን ለማስቀረትና ማህበረሰቡ ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኝ ለማስቻል እየተሰራ እንደሚገኝ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ።

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ተቋማት አሠሪዎች ማህበር የአባላት ጠቅላላ ጉባኤ አካሂዷል።

የግል ጤና ተቋማት ፈዋሽነቱን፣ ጥራቱና ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ለማህበረሰቡ ማድረስ እንዲችሉ የማድረግ ዓላማ ያነገበ ጉባኤ መሆኑን የግል ጤና ተቋማት ማህበር ተወካይ አቶ መንግሥቱ ደምሴ ገልጸዋል።

የህብረተሰቡን የመግዛት አቅም ያማከለ ጥራት ያለው አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ አባላቱ ኃላፊነት ወስደው መስራት እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል።

በግል ጤና ተቋማት የሚከናወኑ ህገ-ወጥ ተግባራትን በማስቀረት ማህበረሰቡ ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኝ እየተሰራ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ጤናና ጤና ነክ ግብአቶች እና አገልግሎት ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን ተወካይ እንዲሁም የክልሉ ጤና ቢሮ ተወካይ አቶ ፍሰሃነ ፍርዴ ገልጸዋል።

በአቋራጭ ለመበልጸግ የሚሰሩ ባለሀብቶች በመኖራቸው በአሰራሩ መሰረት ደረጃውን በመጠበቅ ለማህበረሰቡ ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲሰጥ ሰፊ ስራዎች እየተሰራ ነውም ብለዋል።

አያይዘውም በ2016 ዓ.ም 524 ተቋማት ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰዱን፤ የ12 ተቋማት ፍቃድ መሰረዙን ጠቁመው 82 ሚሊዮን ብር የሚገመት ከደረጃ በታች የተመረቱ መድኀኒት በህገ-ወጥ መንገድ ተይዞ ለማስወገድ መቻሉን ጠቁመዋል።

በህገ ደንብ እና የአሰራር መርህ ላይ ትኩረት ያደረገ ውይይት መካሄዱንም ነው ኃላፊው የጠቆሙት።

በጉባኤው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ተወካይ፣ የማህበሩ ሥራ አስኪያጅን ጨምሮ የዞኖች የግል ተቋማት አመራር እና አባላት ተገኝተዋል።

ዘጋቢ፡ ተዋበች ዳዲ – ከአርባምንጭ ጣቢያችን