“የመሬት ሳንባ”

በደረጀ ጥላሁን

የአማዞን ደን በምድራችን ትልቁ ደን ሲሆን በውስጡ እጅግ ብዙ የእጽዋት እና የእንስሳት ዝርያዎች ያሉበት ነው። ይህ አስደናቂ ክልል የአለምን የዝናብ መጠን በማረጋጋት እና የአየር ንብረት ለውጥን የሚቀንስ ከፍተኛ መጠን ያለው ካርቦን በማከማቸት የአየር ብክለት መጠንን በመቀነሱ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል። እንደ ሲ ኤን ኤን እና የተለያዩ ድረ ገጾች መረጃ አማዞን የአለማችን ትልቁ ደን ሲሆን 40 በመቶ በሚሆኑት 9 የደቡብ አሜሪካ ሃገራት ላይ ያረፈ ነው፡፡ 2/3ተኛው ወይም 60 በመቶው የአማዞን ክፍል የሚገኘው ብራዚል ነው፡፡

አማዞን ሃገር ቢሆን ኖሮ የአለማችን 9ኛው ትልቁ ሃገር ይሆን ነበር፡፡ በአማዞን ደን ውስጥ ከ30 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ የተለያየ ቋንቋ የሚናገሩ ከ2 ሺህ በላይ አባላት ያላቸው 350 ነባር ጎሳዎች ይገኙበታል፡፡ ከ350 ነባር ጎሳዎች መካከል 100 ጎሳዎች እርስ በእርስ ተገናኝተው እንደማያውቁ ነው መረጃው ያመለከተው፡፡ በመረጃው መሠረት አማዞን በአለማችን ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አጥቢ እንስሳት፣ አዕዋፋት እና በደረት የሚሳቡ ፍጡራን የሚገኙበት ደን ነው፡፡

በየሁለት ቀናት ልዩነት አዳዲስ የእጽዋት ወይም የእንስሳት ዝርያዎች በአማዞን ይፈጠራሉ፡፡ 40 ሺህ የእጽዋት እና 1 ሺህ 300 የአዕዋፍ ዝርያዎች በውስጡ ይገኛሉ፡፡ እንዲሁም በጥቅጥቅ ደኑ 400 ቢሊዮን የሚሆኑ ዛፎች የሚገኙ ሲሆን የአለማችንን 20 በመቶ ኦክስጅን ያመርታል፡፡ አማዞን ከ90 እስከ 140 ቢሊዮን ሜትሪክ ቶን ካርቦን በውስጡ በመያዝ የካርቦን ልቀቱን ይቆጣጠራል፡፡ 120 የሚጠጉ የመድሃኒት አይነቶች የሚገኙት ከዚሁ ደን ነው፡፡ አናኮንዳን የመሳሰሉ አደገኛ የእንስሳት ዝርያዎች የሚገኙትም እዚሁ አማዞን ጫካ ውስጥ ነው፡፡

ደኑ ጥቅጥቅ ያለ በመሆኑ እጽዋቱ ጸሃይ የሚያገኙት ከ2 እስከ 5 በመቶ ብቻ ነው፡፡ የመሬት ሳንባ በመባል የሚጠራው አማዞን፤ ከዚህም በላይ በረከት አለው፡፡ አማዞን ደን የ400 ቢሊዮን በላይ ዛፎች መኖሪያ ከመሆኑም በላይ 6.7 ሚሊዮን ስኩዌር ሜትር ሽፋን አለው፡ ፡ አማዞን የአየር ንብረትን ሚዛን በማረጋጋት፣ የውሃ ዑደትን በማስተካከል፣ የዝናብ ስርጭትንና ሙቀትን በመቆጣጠር ለሰብሎች እድገት ወሳኝ ሚና አለው። አማዞን በየዓመቱ በከፍተኛ መጠን ካርቦንዳይ ኦክሳይድ በመምጠጥ ሙቀት ላይ አበርክቶ አለው። በተለይም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀነስና ሙቀትን ለመቆጣጠር የአማዞን ደን ጥቅሙ ከፍተኛ ነው።

አማዞን በዓለም ላይ ትልቁ ደን ብቻ ሳይሆን ከ10 በመቶ ያላነሱ የዓለማችን ብዝሃ ህይወት ያላቸው፣ እፅዋትና እንስሳትን ያካትታል። የአማዞን ወንዝ ከ6 ሺህ 600 ኪሎ ሜትር በላይ የሚፈስ ሲሆን በመቶዎች የሚቆጠሩ ገባር ወንዞች እና ጅረቶች ያሉት በዓለም ላይ ትልቁን የንፁህ ውሃ የዓሣ ዝርያዎችን እንደሚይዝ ከፓንዳ ዶት ኮም ድረ ገጽ የተገኘው መረጃ ያሳያል፡፡ ባለፈው ግማሽ ምዕተ-አመት አማዞን ቢያንስ 17 በመቶ የሚሆነውን የደን ሽፋን አጥቷል፡፡ ግንኙነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስተጓጎለ እና በርካታ ዝርያዎች ለሃብት ብዝበዛ ተዳርገዋል። የተፈጥሮ መኖሪያውን በመለወጥ እና በማሽቆልቆል ላይ የተመሰረተው የአማዞን ኢኮኖሚያዊ ለውጥ እየጨመረ ነው፡፡

ነገር ግን እነዚያ ሀይሎች በጥንካሬ እያደጉ ሲሄዱ፣ አማዞን የአየር ንብረት በክልል እና በአለም አቀፍ ደረጃ በመጠበቅ ረገድ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ ነው፡፡ የአማዞን ሽፋን የሙቀት መጠንን እና እርጥበትን ለመቆጣጠር ይረዳል፡፡ በጫካው ላይ በሚመሰረቱ የሃይድሮሎጂ ዑደቶች አማካኝነት ከክልላዊ የአየር ሁኔታ ጋር በጣም የተቆራኘ ነው፡፡ በአማዞን ደኖች ውስጥ የተከማቸ ከፍተኛ የካርበን መጠን ግምት ውስጥ በማስገባት በአግባቡ ካልተያዘ የአለምን የአየር ንብረት የመቀየር ከፍተኛ አቅም አለ። አማዞን ከ90 እስከ 140 ቢሊየን ሜትሪክ ቶን ካርቦን ይዟል፡፡ የተወሰነው ክፍል እንኳን መለቀቅ የአለም ሙቀት መጨመርን በእጅጉ ያፋጥነዋል።

በአሁኑ ጊዜ በአማዞን ውስጥ ያለው የደን መጨፍጨፍ እስከ 0.5 ቢሊዮን ሜትሪክ ቶን ካርቦን በዓመት ይለቃል፡፡ ከደን ቃጠሎ የሚለቀቀውን ልቀትን ሳይጨምር፡፡ ከኔቸር ኤንድ ካልቸር ኢንተርናሽናል ድረ ገጽ የተገኘው መረጃ እንደሚገልጸው የአማዞን ወንዝ በዓለም ላይ ትልቁን የንፁህ ውሃ ዓሣ ዝርያዎች ይዟል፡፡ የዝናብ ደን የፕላኔቷ እጅግ የበለጸገ እና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የእፅዋት ዝርያዎች፣ ነፍሳት፣ ወፎች እና ሌሎች ሕይወት ያላቸው ዝርያዎች እንዳሉት ያሳያል፡፡ በአማዞን ዙሪያ በሺዎች የሚቆጠሩ የእፅዋት ዝርያዎች በአካባቢው ማህበረሰቦች ለመድኃኒትነት ያገለግላሉ።

ጥናቶች እንደሚያሳዩት አማዞን ለአካባቢያዊ እና ተወላጅ ማህበረሰቦች ብቻ ሳይሆን ለቀሪው አለምም አስፈላጊ የተፈጥሮ ሀብቶች ማከማቻ በመሆን ከረዥም ጊዜ ጀምሮ እውቅና አግኝቷል። የዝናብ ደን የአለምን የዝናብ ሁኔታ በማረጋጋት፣ በከባቢ አየር እና በውሃ ዑደት ላይ እስከ ዩናይትድ ስቴትስ ድረስ ተፅእኖ በማድረግ ወሳኝ ሚና ይጫወታል። በተጨማሪም በውስጡ ያሉ ዕፅዋት ከፍተኛ መጠን ያለው ካርቦን ዳይኦክሳይድ ይይዛሉ፡፡ ይህም የአየር ንብረት ለውጥን ለመቀነስ ይረዳል፡፡ የግብርና መስፋፋት ለዚህ ስነ-ምህዳር ትልቁ ስጋት ነው።

የኢንዱስትሪ እርሻ፣ የከተማ መስፋፋት፣ ማዕድን እና ነዳጅ ማውጣት፣ ግድቦች እና ኃላፊነት የጎደለው የእንጨት ምርትም ከፍተኛ የደን መጥፋት አስከትሏል። ባለፉት 40 ዓመታት ብቻ 20 በመቶውን የአማዞን የዝናብ ደን ጨፍጭፈዋል፡፡ እንዲሁም ተጨማሪ 20 በመቶው የመደምሰስ አደጋ ተጋርጦበታል።

የደን መጨፍጨፍ እየቀጠለ እና የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖዎች እየጠነከሩ በመሄድ ላይ መሆናቸው ይህንን አስደናቂ ስነ ምህዳር ለወደፊት የማጣት ስጋት ይታያል። ስለሆነም አማዞንን ለመጠበቅ እና ዘላቂ የደን ኢኮኖሚ ለማዳበር ከማህበረሰቦች እና አጋሮች ጋር መስራት እንደሚያስፈልግ መረጃው አመላክቷል።