ዩኒቨርሲቲዎች የማህበረሰብ ጉድኝት ሥራዎችን በማጠናከርና ዘላቂ ሥራዎችን በመፈጸም በግብርናው ዘርፍ የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣት መሥራት እንዳለባቸው ተገለጸ

ዩኒቨርሲቲዎች የማህበረሰብ ጉድኝት ሥራዎችን በማጠናከርና ዘላቂ ሥራዎችን በመፈጸም በግብርናው ዘርፍ የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣት መሥራት እንዳለባቸው ተገለጸ

ይህ የተገለጸው የዲላ ‎ዩኒቨርሲቲ በማህበረሰብ ጉድኝት ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር በይርጋጨፌ ከተማ የምክክር ፎረም ባካሄደበት ወቅት ነው።

በምክክሩ የተገኙት ‌‎በትምህርት ሚኒስቴር ከፍተኛ የትምህርት ዘርፍ የምርምርና ማህበረሰብ ጉድኝት ጉዳዮች መሪ ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ሠራዊት ሀንዲሶ፣ ዩኒቨርሲቲዎች የማህበረሰብ ጉድኝት ሥራዎችን በማጠናከርና ዘላቂ ሥራዎችን በመፈጸም በግብርናው ዘርፍ የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣት መሥራት እንዳለባቸዉ ጠቁመዋል።

‎የባለድርሻ አካላት ትስስር መፍጠር የላቀ ሚና እንዳለው በመግለጽ የፎረሙ ተሳታፊ ባለድርሻዎች የሚጠበቅባቸውን በአግባቡ በመወጣት ለዘርፉ ውጤታማነት የበኩላቸውን መወጣት እንዳለባቸውም ሥራ አስፈፃሚው አስገንዝበዋል፡

‎የዲላ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኤልያስ አለሙ፤ ፎረሙ በጌዴኦና በአጎራባች ዞኖች በግብርና ዘርፍ የሚታዩ ችግሮችን ለመቅረፍ በምርምር ለማስደገፍ የተዘጋጀ መሆኑን ገልፀው ዩኒቨርሲቲው የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ለውጥ ለማረጋገጥ የተለያዩ ችግር ፈቺ የምርምር ሥራዎችን እያከናወነ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡

‎በማህበረሰብ አቀፍ አገልግሎት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ በቡና፣ በአፕል፣ በእንሰትና በድንች ምርት በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ዶ/ር ኤልያስ አብራርተዋል፡፡

‎የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የማህበረሰቡ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በአንድ ተቋም ብቻ የሚረጋገጥ ባለመሆኑ፣ በማህበረሰብ ጉድኝት የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ በማሳደግ ችግር ፈቺና እሴት የሚጨምር ተግባራትን ማከናወን እንደሚያስፈልግ ገልፀዋል።

‎ዘጋቢ፡ ዘርሁን ሹፌር – ከይርጋጨፌ ጣቢያችን